Saturday, September 28, 2013

አ ገ ሬ

አገሬ ውበት ነው፣
ለምለምና ነፋስ የሚጫወትበት፣
ፀሃይ የሞላበት፣ ቀለም የሞላበት።
አገሬ ቆላ ነው፣ ደጋ ወይና ደጋ፣
እዚያ ብርሃን አለ ሌሊቱ እስኪነጋ።
አገሬ ተራራ ሸለቆ ረባዳ፣
አገሬ ጅረት ነው ገደልና ሜዳ፣
ውበት ነው በበጋ ፀሃይ አትፋጅም፣
ክረምቱም አይበርድም፣
አይበርድም፣ አይበርድም።
አገሬ ጫካ ነው፣
እንሰሳት አራዊት የሚፈነጩበት፣
በወጥመድ ሳይገቡ ሳይነካቸው ጠላት።
እዚያ አለ ነፃነት፣
በሃገር መመካት፣
በተወላጅነት፣
በባለቤትነት፣
እዚያ አለ ነፃነት።
አገሬ ሃብት ነው፤
ጎመኑ ስብ ጮማ፣ ቆሎ ክትፎ ስጋ፣
ድርቆሹ ፍትፍት ነው፣ ቃሪያው ሙክት ሠንጋ፣
ጠጁ ነው ወለላ፣
ከኮኛክ ያስንቃል የመንደሩ ጠላ።
እህሉ ጣእም አለው እንጀራው ያጠግባል፣
ከቢራ ከሻምፓኝ ውሃው ይጣፍጣል፣
በዓሉ ይደምቃል፣
ሙዚቃው ያረካል፣
ጭፈራው ዘፈኑ ችግርን ያስረሳል።
እዚያ ዘመድ አለ፣
ሁሉም የናት ልጅ ነው፣
ሁሉም ያባት ልጅ ነው፣
ጠላትም አንዳንዴ ይመጣል መቃብር፣
ባለጋራም ቸር ነው “ያገር ልጅ ሲቸገር” ፤
ገነት ነው አገሬ።
ምነው ምን ሲደረግ ?
ምነው ለምን እንዴት ?
ዘራፊ ቀማኛ ምቀኛ ወንበዴ፣
ጥርኝ አፈር በጁ ስንዝር ወሰን አልፎ፣
የተቀደሰውን ያፍሪቃ ላይ ደሴት፣
ባያገኝ ለማርከስ ጠላት ይመኝ እንዴት።
እምቢኝ አሻፈረኝ፣
አሻፈረኝ እምቢ፣
መቅደስ ነው አገሬ፣
አድባር ነው አገሬ፣
እናትና አባት ድኸው ያደጉበት፣
ካያት ከቅደም አያት የተረካከቡት፣
አፈር የፈጩበት፣
ጥርስ የነቀሉበት።
አገሬ ዓርማ ነው፣ የነጻነት ዋንጫ፣
በቀይ የተጌጠ ባረንጓዴ ቢጫ።
እሾህ ነው አገሬ፣
በጀግናው ልጅ አጥንት የተከሰከሰ፣
ጠላት ያሳፈረ አጥቂን የመለሰ።
አገሬ ታቦት ነው ፣ መቅደስ የሃይማኖት፣
ዘመን የፈተነው በጠበል በጸሎት።
ለምለም ነው አገሬ፣
ውበት ነው አገሬ፣
ብሞት እሄዳለሁ ከመሬት ብገባ፣
እዚያ ነው አፈሩ፣ የማማ ያባባ።
ስሳብ እሔዳለሁ ቢሰበርም እግሬ፣
አለብኝ ቀጠሮ ከትውልድ አገሬ።
አለብኝ ቀጠሮ
ከትውልድ አገሬ፣
ካሳደገኝ ጓሮ።
------------(ሰአሊና ገጣሚ ገብረ ክርስቶስ ደስታ) -----------

No comments: