Saturday, September 28, 2013

የጀግና አሟሟት

ምዕራፍ አንድ፡- አጼ ቴዎድሮስ እና ሞት
አትጠገብ የምትባል ሴት ከ195 አመታት በፊት ወንድ ልጅ ወለደች፡፡ ወይዘሮ አትጠገብ ሀይለ ጊዮርጊስ ከሚባል ውድ ባለቤቷ ካሣ የሚባል ልጅ ወለደች፡፡ ልጁ ካሣ ሀይሉ ተብሎ ይጠራ ነበር፡፡ ካሣ ሲያድግ ንጉስ መሆን አማረው፡፡ ካሣ በተወለደበት ዘመን ተራ ሠው አይነግስም፡፡ ነገሥታት የሚሆኑት የሠለሞን ዝርያ ያላቸው፣ በእግዚአብሔር የተመረጡ እና የተሰየሙ እናም የነዚህ ሠዎች ዝርያዎች ነበሩ፡፡ ካሣ ግን ንጉሥ መሆን አማረው፡፡ ሲያስብ እንዲህ እያለ ነበር ፡- “የነገስታቱ ዝርያ አይደለሁም፡፡” “እና ባልሆንስ?!” “አትቆጣ?!” “መቆጣት አይደለም፡፡” “እና ታዲያ;!” “ንጉሥ መሆን አምሮኛል!” “እና ንጉሥ መሆን የምችል ይመስልሃል?!” “Yes, I can” ብሎ ተነሳ፡፡ የአሜሪካው ንጉስ ባራክ ኦባማ `Yes, we can` የሚለውን የምርጫ መወዳደሪያ መፈክር የኮረጀው ከካሳ ሀይሉ ነው፡፡ የምናውቅ እናውቃለን፡፡
ካሳ ጉረኛ አልነበረም፤ በተወለደ በሰላሳ ሰባት አመቱ፣ ዳግማዊ ቴዎድሮስ ተብሎ በደረስጌ ማርያም ቤተ-ክርስቲያን ንጉሰ ሆኖ ተቀባ፡፡ ካሳ ተራ ንጉስ አልነበረም፤ ሀገሩን በጣጥሰው ሲገዙ የነበሩትን ቅርብ ሀሳቢ መሳፍንት አስገብሮ ንጉስ ነገስታቸው ሆነ፡፡ ያልተረጋጋች እና ያልሰለጠነች ኢትዮጵያን ለማረጋጋት እና ለማሰልጠን ጣረ፤ ለአስራ ሶስት አመታት ነገሰ፤ ባከነ፡፡ ከንግስናው እለታት አንድ ቀን መሞቻህ ይሁን ሲለው፣ እኩያው አድርጎ ለሚያስባት የእንግሊዝ ንግስት የቴክኒክ ድጋፍ የሚጠይቅ ደብዳቤ ፃፈ፤ ፅፎም ካሚሮን ለሚባል እንግሊዛዊ፣ እንዲያደርስ ላከው፡፡ መልእክተኛው ግን የቁራ መልእክተኛ ሆነ። ካሜሮን የተላከውን መልእክት ሳያደርስ፣ በዚያም ላይ ግብፅ ምናምን ሲዞር ከርሞ መጣ፤ በወቅቱ የግብፅ ሰዎች ከቴዲ ጋር አሪፍ ጓደኞች አልነበሩም፡፡ ካሜሮን መጣ፡፡
“እህሳ ነጫጭባው! መልእክቴን ለንደን አደረስሽ?” “አላደረስኩም ነብሴ፤ ግን እንዲደርስ በሌሎች ልኬያለሁ፡፡” “እኔ እኮ መልእክቱን አንቺ እራስሽ ለንደን ወስደሽ ለንግስቲቷ በእጇ እንድታስረክቢ ነው የላኩሽ፡፡” “ፍሬንድ እኔ እሱ መች ጠፋኝ፤ አለቆቼ እኛ በምናደርሰው መንገድ እናደርሰዋለን አሉኝ እንጂ፡፡” “እና ይህን ሁሉ ጊዜ ምን ስታደርጊ ከርመሽ መጣሽ?!” “ግብፅ ምናምን ለአንዳንድ ጉዳዮች ሄጄ ነበር፡፡” “እንዲህ ነኝና መይሳው!” አለ ንጉስ ቴዎድሮስ፤ በጣም ተናዷል ፡፡ “ይህችን ነጫጭባ አስገባት፡፡” ካሜሮን እስር ቤት ገባ፤ ታሰረ፡፡ የካሜሮን አቢሲኒያ ውስጥ መታሰር ለንደን ተሰማ፡፡ እንግሊዝ ካሜሮንን ለማስፈታት ራሳም የሚባል ሰውዬ ላከች፤ ቴዲ እሱንም ጭፍራዎቹንም አሰራቸው፡፡
ቴዲ ሳይታወቀው አንገቱ ላይ ገመዷን እያጠበቀ ነበር፡፡ ቴዎድሮስ የታሪካችን ፈርጥ፣ የስነ-ፅሑፋችን ጌጥ ነው፡፡ እስከአሁን ካነበብኳቸው የአማርኛ መፅሐፍት የብርሃኑ ዘርይሁንን “የታንጉት ምስጢር” የሚያክል የለም፡፡ ቴአትር ብዙ አላየሁም፣ ካየኋቸው ግን የፀጋዬ ገብረ መድህንን “ቴዎድሮስ” የሚስተካከል የለም፡፡ ምዕራፍ ሁለት፡- እኔና ሞት የአንድ ሠው የህይወት ዘመን ሶስት ክፍሎች ናቸው ያሉት፡፡ አንድ፡- ጅማሮ፤ ሁለት፡- ኑሮ፤ ሶስት፡- ሞት፡፡ ሶስቱም እኩል ዋጋ አላቸው፡፡ ቴዎድሮስ ከህይወቱ አጀማመር እና አኗኗር በጣም ጎልቶ የሚነገረው አሟሟቱ ነው፡፡ የጀግና አሟሟት ተምሳሌት ተደርጎ ሁሌ ነው የሚወራው፡፡…. እኔ ደግሞ ብዙ ጊዜ ያልተሳኩ እራስን የማጥፋት ሙከራዎች አድርጌያለሁ፤ እንደ ሲልቪያ ፕላዛ። ሲልቪያ ፕላዛ ሶስት የከሸፉ እራስን የማጥፋት ሙከራዎች አድርጋ፣ በሶስት መክሸፍ አንድ የተሳካ ግጥም ፅፋለች፡፡ የከሸፉ እራስን የማጥፋት ሙከራዎች ትዝ ባሉኝ ጊዜ (ሁሌ ነው ደግሞ ትዝ የሚሉኝ) ቴዎድሮስ ትዝ ይለኛል፡፡ እራስህን ማጥፋት የምር እየፈለክም ላይሳካልህ ይችላል፡፡ ቴዎድሮስ ደፋር ብቻ ሳይሆን እድለኛም ነበር። ሁሌ ስለ ቴዎድሮስ አስባለሁ፤ ሁሌ ትዝ የሚልህ ምርጥ መጽሐፍ “የታንጉት ምስጢር” ከሆነ፤ ያው ቴዎድሮስ ነው ትዝ የሚልህ፡፡ አንድ ቀን ስለህይወት ከንቱነት እያሰብኩ፤ (ቀጣዩን ራሴን የማጥፋት ሙከራዬ የመግቢያ ሀሳብ ነው፤ ከልምድ አውቃለሁ) የሚገርም ነገር ተከሰተ፡፡ የቴዎድሮስ አይነት የክብር አሟሟት ተከስቶ አየሁ። የሚገርመው ደግሞ ብዙ ሠው ተሰብስቦ በነበረው ባር ድርጊቱን ከመጀመሪያው እስከመጨረሻ ስከታተል የነበርኩት እኔ ነኝ፡፡ ለኔ የተላከልኝ መለኮታዊ መልእክት ይመስለኛል፡፡ ቴሌ ባር የሚባል ቤት ውስጥ የመቅደላ ታሪክ ሲደገም፤ ሙሉ(!) ታሪኩን ያየሁት እኔ ብቻ ነበርኩ። ታሪክ መፃፍ አለበት፤ በተለይ እንዲህ አይነቱ፡፡ የክስተቱ ሙሉ ተመልካች (ነበርኩ) ነኝ ብያለሁ። አሁን የምፅፍላችሁ ግን ድርጊቱ ከተከሰተ በኋላ ስለ ሠዎቹ ያጠናከርኩትን አካትቼ ነው፡፡
                                                         * * *
ሲልቪያ ፕላዝ እራሷን እንስቲቷ አልአዛር እያለች ነው የምትጠራው፤ ብዙ ጊዜ ከሞት ተርፋለች፤ ተነስታለች፡፡ እራሳቸውን ለማጥፋት ሞክረው የዳኑ ሠዎች ከሞት እንደተረፉ ሳይሆን ከሞት እንደተነሱ ነው የሚሰማቸው፡፡ የምናውቅ እናውቃለን፡፡ ሲልቪያ ፕላዝ Lady Lazarus በሚለው ግጥሟ ላይ እነኚህ ስንኞች አሉ፡- I have done it again One year in every ten I manage it… Soon, soon the flesh The grave cave ate will be At home on me --- I am only thirty And like the cat I have nine times to die. This is Number three What a trash To annihilate each decade --- The first time it happened I was ten It was an accident The second time I meant To last it out and not come back at all I rocked shut Dying Is an art, like everything else I do it exceptionally well. I do it so it feels like hell I do it so it feels real I guess you could say I’ve a call. ሲልቪያ ፕላዛ በአራተኛ የተሳካ ሙከራዋ፤ በ31 አመቷ ሞተች፡፡ ጠፋች፡፡
እራሷን አጠፋች፡፡ ምዕራፍ ሶስት፡- ዘመናዊው አጼ ቴዎድሮስ እንደተለመደው ጠዋት ከእንቅልፌ ነቃሁ፡፡ አምሽቼ ተኝቼ በጠዋት ነው የምነቃው፡፡ እንቅልፍ አይወደኝም፡፡ ለዚያም ይመስለኛል ሞት የሚጠላኝ። በሁለት ታክሲ ወደ ሰንጋተራ ሄድኩ፣ ወደ አረቄ ቤት፡፡ የአረቄ ቤት የጠዋት ጓደኛዬ አስፋው ቀድሞኛል፤ ቁርስ አብረን ነው የምንበላው፤ ማታ ማታ አስር አስር ብር አዋጥተን ለአረቄ ቤቱ ባለቤት እንሰጣለን፤ ጠዋት ጉበት ገዝቶ፤ ከትፎ፣ ቀምሞ ይጠብቀናል፤ አብረን እንበላለን፡፡ ዛሬ ሠኞ ነው፡፡ ሰኞ ይደብራል፡፡ (አጼ ቴዎድሮስ የሞተው ሰኞ ቀን ነው፤ በፋሲካ ማግስት፡፡) ዛሬ ሠኞ ነው፡፡ ዛሬ ቀፎኛል፡፡ (የዛሬው ቁርስ ከአስፋው ጋር የመጨረሻችን ይሆናል፤ አስፋው በንጋታው ይሞታል፡፡ አስፋውም ቀፎታል፡፡ በቅርቡ እንደሚሞት እንደታወቀው ያስታውቃል፡፡) ቁርሴን ከነ አስፋው ጋር በልቼ፣ አንድ አረቄ ጠጣሁ፡፡ አካሄዴ የተለመደ ነው፡፡ ጠዋት ቁርስ እበላለሁ፣ አረቄ እጠጣለሁ፣ ከዚያ ውሃ ያስፈልገኛል (ጠላ ወይ ድራፍት) ማለቴ ነው፡፡ ዛሬ ብር አለኝ፤ ድራፍት መጠጣት እችላለሁ፡፡
ወደ ቴሌ ባር ወረድኩ፡፡ በነገራችን ላይ በ dehydration እራስን ማጥፋት ይቻላል፤ በየእለቱ dehydrate የሚሆን ሰውነቴ ጠዋት ሁሌ ውሃ ይለኛል፡፡ ውሃ መጠጣት አልችልም፤ ጠላ እና ድራፍትን እንደውሃ ነው ሠውነቴ የሚጠቀማቸው፡፡ በ dehydration እራስን ማጥፋት ይቻላል፡፡ ከሰውነታችን ሰባ ከመቶው ውሃ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ አስራ አምስት በመቶ ብናጎል እንሞታለን፡፡ (ምናልባት ቀጣዩን ራሴን የማጥፋት ሙከራ የማደርገው በ dehydration ይሆን ይሆናል። ሌላም አማራጭ አለ፤ የከሰል ጭስ፤ ለምሳሌ ዘንድሮ ብቻ በከሰል ጭስ አዲስ አበባ ውስጥ አስራ አንድ ሰው ሞቷል፤ ስለዚህም አስብበታለሁ፡፡) ወደ ቴሌ ባር ሄደኩ፡፡ ውሃ ፍለጋ፡፡ የመጠጫ፣ የመጫወቻ፣ የመተከዣ፣ የመደንዘዣ፣ የማንበቢያ፣ የመፃፊያ ... የተለመደች ቦታ አለችኝ፡፡ እዚያ ቦታ ላይ ልቀመጥ ስል እልፍ ብሎ ያለው ወንበር ላይ ተአምር አየሁ፡፡ ውብ ሴት! ሌላ ገለፃ አያስፈልግም፡፡ ውብ ሴት፡፡
የተቆጣች ፀይም ውብ ሴት! ከሰው ጋር ናት፡፡ ወይ ከባሏ ጋር፣ ወይ ከጓደኛዋ ጋር፣ ወይ ከፍቅረኛዋ ጋር ናት፡፡ በሱ ነው የተቆጣችው፤ እሱን ነው የምትቆጣው፡፡ የተለመደ ቦታዬን ትቼ እነሱ አጠገብ ያለውን ወንበር ስስብ አንድ እጅ አብሮኝ ወንበሩን ሳበ፡፡ ሁለታችንም ልጅቷን እያየናት ስለነበር አልተያየንም፡፡ ወንበሩን አጥብቄ ያዝኩት። ልጅዬው በልመና አይነት አየኝ፡፡ በቁጣ አየሁት፡፡ አይኑን ቢያንከራትት ልጅቷ አጠገብ ምንም ወንበር የለም፡፡ ፈልጎ ሊያገኝ የቻለው ልጅቷ ፊት ለፊት ራቅ ብሎ ያለ ወንበር ነው፡፡ ወደዚያ አመራ፡፡ ከዚያ ትታየዋለች፤ ትርቅበታለች እንጂ ትታየዋለች፡፡
ልክ ልጅዬው ወንበሩን ለቅቆልኝ ሊሄድ ሲል፡- ልጅቷ እንዲህ ስትል ሰማናት፡- “እንዴት እንደዛ ታደርጋለህ;! የገዛ እህቴን;! እራሴ አልጋ ላይ;!” ወንበር እየተሻማኝ የነበረው ሰው ከርቀት ልጅቷን ሊያሳየው የሚችለው ወንበር ሊያዝበት ሲሆን እየሮጠ ሄደ፡፡ እውነት እሮጧል፡፡ “እህስ;” አለችኝ አለም አስተናጋጇ፤ የምንኖርባት አለም ብታስጠላኝም ይህቺ አስተናጋጇ አለም ግን ደስ ትለኛለች፤ እወዳታለሁ፡፡ “ድራፍት፡፡” አለም ድራፍቱን ልታመጣ ሄደች፡፡ ፊልም ላይም፣ መጽሄት ላይም፣ ምድር ላይም ይህችን የተቆጣች ጠይም የምትመስል ቆንጆ አይቼ አላውቅም፡፡ የተናገረችውን ስሰማ ግን ማመን አቃተኝ፡፡ አሁን የገረመኝ አብሯት ያለው ሠው ነው፤ እሷ አይደለችም፡፡ ምን አይነት ጀግና፣ ወይ ሠይጣን፣ ወይ መልአክ ቢሆን ነው ይህቺን ሴት ትቶ አልጋዋ ላይ እህቷን የሚዳራው;! አሁን ደግሞ አብሯት ቁጭ ብሎ እያወራ ነው፡፡ አየሁት፡፡ ግድየለሽ ነው፤ የእግዚአብሔር ግድ የለሽነት ይታይበታል፡፡ እያጨሰ ነው፤ እንደ ሰይጣን ነው የሚያጨሰው፡፡

              “ይኸውልሽ እህትሽ ሁሌ እንደምታስቸግረኝ ታውቂያለሽ፡፡ እንድታሳርፊልኝ ደጋግሜ ነግሬሻለሁ፤ የምሬን ነበር፤ አንቺን እንዳይደብርሽ ብዬ ነው ግን፤ ለሌላ አይደለም፤ ግድ እንደሌለኝ ታውቂያለሽ፤ እንኳን ነገር ፈልገውኝ እንዲሁም እንዲያው ነኝ፡፡” “ግን እህቴን;! አልጋዬ ላይ;!” “ምን ሆነሻል;! ሌሎች ሴቶች እንደማወጣ ታውቂያለሽ! እህትሽ መሆኗ ምን ለውጥ ያመጣል;! አንቺ እንዳይደብርሽ እንድታሳርፊልኝ ነግሬሻለሁ፤ … እህቴን ብሎ ነገር! በጣም ብዙ እህትማማቾች ተኝቻለሁ፤ እያወቁም በድብቅም፡፡” “እሺ አልጋዬ ላይ;!” “ቦታው ምን ለውጥ ያመጣል; አልጋሽ ላይ ሆነ፣ ሆቴል ሆነ፣ ጫካ ውስጥ ሆነ፣ ቢሮ ውስጥ ሆነ፣ ምን ለውጥ ያመጣል;” እነዚህ ቦታዎች ሁሉ ላይ እህቷን ተኝቷታል፡፡ ያስታውቃል፤ አውቆ ነው ቦታዎቹን የቆጠረላት፡፡ ትወደዋለች፡፡ እንደማታሸንፈው ታውቃለች፡፡ እሱ ሌላ ሲጋራ ለኮሰ፡፡ እሷ በተቆጡ አይኖቿ አሻግራ ታይ ጀመር፡፡ ቅድም ከኔ ጋር ወንበር ሲናጠቅ የነበረው ሰው ሲወራጭ አየችው፡፡ ለሷ ነው የሚወራጨው፡፡ በእጁ ምልክት “እሱን ተይው…” “ወድጄሻለሁ…” “ነይ ወደኔ…” አይነት ምልክቶች አሳያት፡፡ ዝም አለችው፡፡ ምልክቶቹን ደጋገማቸው፡፡
“ግድየለሽም እሱን ተይው…” “በጣም እወድሻለሁ…” “ነይ ወደኔ…” እሷም በምልክት እና በንዴት “ከሠው ጋር ነኝ እኮ” አይነት አለችው፡፡ በምልክት እንዲህ ማውራት የሚቻል አይመስለኝም ነበር፡፡ ተችሎ እያየሁ ነው፡፡ ቋንቋው በግልፅ እየተሰማኝ፡፡ ወዲያ ማዶ የተቀመጠው ሠው፡- የሰማውን ሰምቷል፡፡ “ድንቄም ከሠው ጋር!” አይነት ምልክት አሳያት፡፡ የሰማውን ሰምቷላ፡፡ እሷንም አብሯት ያለውንም ሠው የሚያጣጥል ምልክት አሳያት፡- “ደግሞ እንዲህ እያደረገሽ!” የሚል አይነት፡፡ አይኗን ከሰውየው ላይ አነሳች፡፡ አብሯት ያለው ሠው እያጨሰ ነው፡፡ አያያትም። ጭሱ ውስጥ እህቷን እያየ ይመስላል፡፡ አሁን ወዲያ ማዶ ስላለው ሠውዬ እናውራ፡፡ ጨዋ ወልዶ ጨዋ ያሳደገው ነው፡፡ አባቱ ኮሎኔል ናቸው፡፡ ልጃቸውን ያሳደጉት እሳቸው ከኖሩበት ሙያ በጠነከረ ዲሲፕሊን ነው፡፡ የስኬት ሶስቱ ስላሴዎች የታደሉት ሠው ነበር፡፡ ለተሳካ ህይወት የሚያስፈልጉት ሶስት ነገሮች ናቸው magic, method, reason, (የአእምሮ ጥሬ ብቃት፣ ትጋት እና በምክንያት መመራት ልንላቸው እንችላልን) እሱ ሶሰቱንም ተጎናጽፏል፡፡ ሶስቱም ነገሮች ብዙ ጊዜ አብረው አይከሰቱም፤ የአእምሮ ምርጥ ጥሬ ብቃት እያለህ ሰነፍ ልትሆን ወይም በምክንያት የማታምን ልትሆን ትችላለህ፡፡) ልጅ እያለ ጎበዝ ተማሪ ብቻ አልነበረም፡፡ በሁሉም ጨዋታዎች አንደኛ ነበር፡፡
ፈጣን ሯጭ፣ አብዶ የሚችል ኳስ ተጫዋች፣ በአንድ ጠጠር አራት በልቶ ባንዴ የሚነግስ ዳማ ተጫዋች፣ በአምስት ስድስት እርምጃዎች check mate ላይ የሚደርስ ቼስ ተጫዋች ነበር፤ ገና በልጅነቱ፡፡ ዩኒቨርሲቲ በማዕረግ ገብቶ፣ በማዕረግ ተመርቆ ወጣ፡፡ ስራ ያዘ፡፡ መኪና ገዛ፡፡ ቤት ገዛ፡፡ ለወላጆቹ ብቻ ልጅ ነው፡፡ እናት እና አባቱ እሱን ሲያዩ ሁሌ እንባ ይተናነቃቸዋል፤ የደስታ እንባ፡፡ ሁሌ እሱን ሲያዩት የደስታ እንባ በአይናቸው ግምጥ ይላል፡፡ ገና ፍቅር ምን እንደሆነ ሳያውቅ የፍቅር ደብዳቤዎች ይደርሱት ነበር፤ ገና የሰባተኛ ክፍል ተማሪ ሆኖ የተጻፈለትን የፍቅር ደብዳቤ ለአባቱ ወስዶ አሳያቸው፤ ሳቁ አባቱ፡፡ “መጥፎ ነገር አይደለም፤ ግን ጊዜው ገና አልደረሰም፡፡” አሉት፡፡ “እሺ አባባ፡፡” አለ፡፡ ጊዜው መቼ እንደሚደርስ ግን አልነገሩትም፡፡ “ሌሎች እንዲህ አይነት ደብዳቤዎች ሲደርሱህ አሳየኝ፡፡” “እሺ አበባ፡፡” የተጻፉለትን ሁሉ ለአባቱ አቀበለ፡፡ ኋላ ላይ አባቱ ማንበብ ታክቷቸው፣ እየተቀበሉት ጣሏቸው።… ዘንድሮ ስራ ከያዘ አምስተኛ አመቱ ነው፡፡ ከሴት ጋር ታይቶ አይታወቅም፡፡ የተደላደለ ኑሮ እና ምርጥ ዘር የሚፈልጉ ሴቶች ሁሉ በግልፅም በስውርም ለትዳር ወይ ገፋፍተውታል ወይ ጠይቀውታል፡፡
አባት እና እናት አሁን መፍራት ጀመሩ፡፡ አሁን ልጃቸው ትዳር ይዞ ማየት ይፈልጋሉ፡፡ ቤተሰቦቹ የሚወዱትን ያህል ልጃቸውን ይፈሩታል፡፡ እንከን የለሽ ነው፡፡ አባቱ አንድ ቀን እየፈሩ፡- “የሚመችህ ከሆነ እራት ልጋብዝህ ዛሬ፡፡” አሉት፡፡ “እሺ አባባ፤ ይመቸኛል፡፡” እራት ጋበዙት፡፡ “አባባ የሆነ ያሳሰበህ ነገር ያለ ይመስላል!” “አዎ ልጄ፡፡” “ምንድነው;” “አንተ ነህ ዳግም፡፡” ስሙ ዳግማዊ ነው፡፡ “እንዴ አባባ;! እኔ;!” “አዎ ዳግሜ፡፡” “ምን አጠፋሁ;” “ኸረ ምንም፤ ትዳር፣ ትዳር ነው፤ ለምን ትዳር አትይዝም;” ቅልል አለው፤ አባትም እንዲሁ፡፡ “የሚገርምህ አባባ እኔም እያሰብኩበት ነበር፤ ግን አዋይሀለሁ እያልኩ ትንሽ አፍሬ ነው የተውኩት፤ እንጂ ሰሞኑን እቤት ስመላለስ የነበረው ይህንኑ ላዋይህ ነበር፤ እንዴት እንደማወራህ ግራ ገብቶኝ ነው የተውኩት፡፡” አባት የደስታ እንባ በአይናቸው ግጥም አለ፡፡ “ምኑ ነው ግራ የገባህ;” “ምን አይነት ሴት ነው ማግባት ያለብኝ የሚለው ነዋ!” “ይኸማ በጣም ቀላል ነው፤ ማግባት ያለብህ የምታፈቅራትን ሴት ነው፤ እና የምታፈቅርህን፡፡ እኔ እና እናትህ አርባ አምስት አመት በፍቅር እና ያለ አንዳች ኮሽታ የኖርነው ስለምንፋቀር ነው፤ እናትህን ያገባኋት አፍቅሬያት፣ እንደምታፈቅረኝ ካረጋገጥኩ በኋላ ነው፡፡ ፍቅር ካለ ሌላው እዳው ገብስ ነው፡፡” አባት እና ልጅ በደስታ እና በፍቅር ተያዩ፡፡ ተጨባበጡ፡፡ ልጅ ሲያስጨንቀው የነበረው ጥያቄ ተመለሰለት፡፡ አባትም ሲያስጨንቃቸው የነበረው ነገር እንዲህ በቀላሉ ሲፈታ እንደ ልጅ ሆኑ፡፡ የደስታ እንባ በአይናቸው ግጥም አለ፡፡ ሲለያዩ ዳግም አባቱን አቅፎ እንዲህ አላቸው፡- “እማማን በቅርቡ ለሰርግ ተዘጋጂ በላት፡፡” አባት መኪናቸው ውስጥ የደስታ ለቅሶ አለቀሱ። ዳግማዊም አለወትሮው እየደነሰ ነበር የመኪናውን በር የከፈተው፡፡ ማግባት ያለብህ የምታፈቅራትን ነው! አለቀ፡፡ ለካ እንዲህ ቀላል ነበር፡፡  
                                                 * * *
አሁን ወደ ቴሌ ባር እንምጣ፡፡ ዳግማዊ ልጅቷን እንዳየ አፍቅሯታል፡፡ ደግሞም አብሯት ያለዉ ሰዉ ያላትን ሰምቷል፡፡ አድርጎት የማያውቀውን እያደረገ ያለው ልጅቷን ስላፈቀራት ነው፡፡ አፍቅሮ አያውቅም፤ እና ምን እና እንዴት ማድረግ እንዳለበት አያውቅም፡፡ ግን ስህተት እያደረገ እንዳይደለ ታውቆታል፡፡ ልጅቷን አፍቅሯታል፡፡ ይሄ 1 + 1 ነው፤ እውነት። ልጅቷ ደግሞ እህቷን እራሷ አልጋ ላይ ከሚተኛ ሰውዬ ጋር ናት፤ ይሄ እድል ነው፡፡ እውነት + እድል, ስኬት ልጅቷ እህቷን የተኛባትን ሰውዬ፡- “ልጃችንስ;” አለችው በሚያሳዝን እና በሚለማመጥ ድምጽ፡፡ “ልጃችንስ; የምን ልጃችን ነው;! ልጃችን የሚባል ነገር የለም፤ ልጁ ያንቺ ነው፤ እኔ ልጅ የለኝም፡፡ በመጀመሪያም ነግሬሻለሁ፤ እኔ ልጅ አልፈልግም። በምድር ላይ ልጅ እንደመውለድ ወይም ለዚያ ተባባሪ እንደመሆን ያለ ቀፋፊ ሀጢያት እንደሌለ ነግሬሻለሁ፤ አትስሚም ግን፤ ወይም አላመንሽኝም፤ እኔ አልዋሽም፡፡ በሀጢአቴ አታስሪኝም፡፡ እኔ ፤ልጅ መውለድ ሀጢአት መሆኑን ነግሬሽ እየተጠነቀቅኩ ነበር፤ አንቺ ተሳሳትሽ፡፡ ሀጢአቱ ያንቺ ነው፤ ልጁ ያንቺ ነው፡፡ ነግሬሻለሁ፡፡” ነግbታል፡፡ ተስፋ በመቁረጥ አይኗን ወደ ማዶ አማተረች፤ ዳግማዊ ይወራጫል፡፡ “ግድ የለሽም እሱን ተይው…” “በጣም እወድሻለሁ…” “ነይልኝ እና አብረን እንኑር..” ተናደደች፡፡ “እንዴት ማየት ይሳነዋል;! ምንም ይሁን ከሰው ጋር ነኝ! ምን ሆኗል ልጁ;! እንዲህ አይነት ሰዎች ናቸው ሰው በሰላም አብሮ እንዳይኖር የሚያደርጉት! እህቷን ወደተኛባት ፍቅረኛዋ አየች፡፡
አያያትም፤ እያጨሰ ነው፡፡ “ስማ!” አለችው፡፡ አያት፡፡ “እግዜርን እንኳ አትፈራም;!” ከት ብሎ ሳቀ፡፡ ደስ የሚል ሳቅ፡፡ “እግዜር ! እግዜርን አትፈራም;! እግዜርን እኔን መፍራት አለበት፤ ደሞ እንደሚፈራኝ እርግጠኛ ነኝ። ይሄውልሽ እኔ እግዜርን ባገኘው፤ ሮበርት ዲኔሮ እንዳለው you have a lot of explaing to do ምናምን አይነት ቀሽም ነገር አይደለም የምለው!….” አቋረጠችው፡፤ ንዴቷ እና ንቀቷ በጣም፣ በጣም፣ በጣም ያስፈራል፡፡ አብሯት ያለው ሠውዬ እያያት ስለማያወራ አላያቸውም፡፡ “ምን ነበር የምለትለው;” አለችው በቁጣ፣ በንዴት እና በንቀት፡፡ “አናቱን ነበር የምለው፡፡” በርጋታ የምትጠጣውን ቢራ አነሳች፤ ተነስታ ቆመች፤ አናቱን አለችው፡፡ ጠርሙሱ አናቱ ላይ ተሰበረ፡፡ (እግዚአብሔር ሰውየው ያለውን ሠምቶ ተናዶ ይሆን እንዴ;) አሻግራ አየች፡፡ አሁን ዳግማዊ ክው ብሎ እያያት ነው፡፡ የተሰበረውን ጠርሙስ ይዛ በቀስታ ዳግማዊ ወዳለበት ወንበር መራመድ ያዘች፡፡
ምን ልታደርግ እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡ ዳግማዊ በአባቱ ምክር የታጠቀውን ሽጉጥ አወጣ፡፡ “እዛው ሁኚ፤ እንዳትጠጊኝ፡፡” እንደማይተኩስ አውቃለች፤ ጆን ስቴንቤክ ፈረስ እና ሴቶች፣ ወንዶች (ጋላቢዎቻቸው) እርግጠኛ ሲሆኑ እና ሲያመነቱ በእርግጠኝነት ያውቃሉ ብሏል፡፡ “እተኩሳለሁ፤ እውነቴን ነው፡፡” በቀስታ እና በእርጋታ ተራመደች፡፡ “እ-ተ-ኩ-ሳ-ለ-ሁ፡፡” አሁን እውነቱን እንደሆነ ገብቷታል፡፡ የሽጉጡ አፈሙዝ ወዴት እንደዞረ አላየችም፡፡ መሞት ፈልጋለች፡፡ መሰንዘር የምትችልበት እርቅት ላይ ስትደርስ የተኩስ ድምጽ ተሰማ፡፡ ፊቷ በደም ተሸፈነ፡፡ ጠርሙስ ባልያዘው እጇ ደሙን ከፊቷ ላይ ጠረገች፡፡ ዳግማዊ ሽጉጡን በአንድ እጁ እንደያዘ ተጋድሟል፡፡ እራሱን አጥፍቷል፡፡ ጀግና፡፡ ማን በሴት እጅ ይሞታል;! እኔ አሁን እራሴን ማጥፋት አልፈልግም፡፡ ለመኖር ምክንያት አግኝቻለሁ፡፡ አንድ፡- ያቺን ልጅ እስር ቤት እየሄድኩ ሁሌ እጠይቃታለሁ፡፡ ሁለት፡- ልጇን አሳድጋለሁ፡፡

No comments: