Thursday, February 27, 2014

የአርሲ ጉዞዬ አስደናቂ ማስታወሻ

                                                                                              Written by  ነቢይ መኮንን

 ከ38 ዓመት በኋላ ከመቃብር የወጣው አስከሬን ትርዒት

የፊዚክስ ባለሙያው የዶ/ር ሙሉጌታ በቀለ አባት የፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ አስከሬን እንዴት ተገኘ? ዝርዝሩ ብዙ ነው፤ ጉዳዩ ግን ተዓምር ተባለ!

ወደ አርሲ አሰላ - ሳጉሬ መንገድ የጀመርነው ቅዳሜ የካቲት 8 ቀን 2006 ዓ.ም ከንጋቱ ለአንድ ሩብ ጉዳይ ነው፡፡
ከናዝሬት .. ወደ ሶደሬ አቅጣጫ … መልካሰዲ ስንደርስ ወደ ቀኝ ዞረን ዴራ፣ ኢቲያን አልፈን በብቅል ፋብሪካ አድርገን አሰላ ገባን፡፡ ከዚያ ወዲያ እንግዲህ ከ 23 ኪ.ሜ በኋላ ሳጉሬ ወረዳ ልንሄድ ነው፡፡
ወደ ሳጉሬ ከመሄዳችን በፊት ወደ አሰላ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን መሄድ ዋንኛው የመርሀ-ግብሩ መነሻ ነው፡፡ ለምን? ታሪኩ እዚህ ጋ ይጀምራላ፡፡
38 ዓመት የፈጀው አስከሬን ለምን ይሄን ያህል ጊዜ ፈጀ? ሂደቱ ምን ይመስላል? ከመጨረሻው ትርዒት ጀምረን ወደ ኋላ 38 ዓመት እንጓዛለን፡፡

ከአሰላ ሚካኤል ቤተ ክርስሪያን አስከሬኑን ይዘን ወደ ሳጉሬ ሥላሴ ቤተክርስቲያን ወደ ፊታውራሪ በቀለ ኦጋቶ ትውልድ አገር እየተመምን ነው። ከ100 በላይ መኪና እንደሰንሰለት ተቀጣጥሎ ነው የሚሳበው፡፡ አስከሬኑ በፒካፑ መኪና ነው የተጫነው፡፡
የሳጉሬ ፖሊሶች በተጠንቀቅ መሆናቸው አያጠራጥርም፡፡ በፒካፓቸው አጀቡን እየተቆጣጠሩ ፊት ኋላ ይላሉ፡፡ በአብዛኛው መሪዎቹ እነሱ ናቸው!
ገና ወደ ሳጉሬ ወረዳ መዳረሻ ስንደርስ፤ ከመቶ በላይ ፈረሰኞች ተቀበሉን፡፡ ግማሹ “ጌታዬ! ጌታዬ!” ይላል፡፡ ግማሹ “አምሣ ቢወለድ አምሳ ነው ጉዱ
አምላክ ካበጀው ይበቃል አንዱ!” ይላል፡፡
ሌላው ያቅራራል፡፡ ሌላው ይፎክራል፡፡ ጉድ ነው የሚታየው! ዛሬ ትኩስ ሬሳ የሚቀብር እንጂ የ38 ዓመት አፅም ስብርባሪ ተሰብስቦ፣ እንደ ሙሉ አስክሬን ታስቦ፤ ሊቀብር የመጣ አይመስልም!
አንድ የዘመነ ብሉይ-(ክላሲካል) ፊልም የማይ ነው የመሰለኝ፡፡ የፈረስ ግልቢያ ጥበብና የስሜታዊ ንዝረታቸው ህያውነት እጅግ አድርጎ አስደምሞኛል።
ወደ ከተማው ስንዘልቅ እንደገና የፈረሰኛው ቁጥር ጎላ፡፡ ህዝቡ በነቂስ ወጥቶ ግራና ቀኝ ይጠብቀናል። በቀበሌ ጥሩምባ፣ በመንግሥት ትዕዛዝ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶት እንጂ የሟቹ ሀዘን ከ38 ዓመት በኋላ ልቡን ነክቶት ነው ለማለት ይቸግራል! ሽለላ፣ ለቅሶ፣ ፉከራ… ድብልቅልቁ ወጥቷል፡፡
ከ38 ዓመት በኋላ የተገኘው አስከሬን ታሪክ፤ ዛሬ ነብስ ዘርቶ እየተነሳ ነው፡፡ የፊታውራሪ በቀለ ኦገቶና የሌሎች የ16 አፅሞች ሰብስብ የቀብር ቀን! በደርግ መንግስት በግፍ ተገድለው የትም የተጣሉ 17 ሰዎች ታሪክ ትንሣዔ! በሺዎች የሚቆጠር ህዝብ ያጀበው የፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ አፅም ወደ መጨረሻ ቦታቸው ሲጓዝ ማየት በእውነት ተዓምር ነው! ለዐይን ማረፊያ የሌለበት ህዝብ ብዛት ለጉድ ይታያል፡፡
የካሜራ ባለሙያዎች እየበረሩ በመኪና ቁመት እየማተሩ ይቀርፃሉ፡፡
ወደ መቃብሩ ቦታ የሚተመውን ጉንዳን ህዝብ፣ ቁጥሩንም ሆነ ነገደ- ጉንዳን ጉዞውን መተለም አይቻልም።
አፋፉ ላይ፣ ትልቅ የብረት ወንፊት ሳጥን የመሰለው የመቃብር ቤት በጉልህ ይታያል፡፡
ወጣቶች ባካባቢው ባለው ዛፍ አናት ተንጠላጥለው ስነ-ስርዓቱ ቁልጭ ብሎ እንዲታያቸው ዐይናቸውን ቁልቁል ወደ መድረኩ ሰክተዋል፡፡
የሚገርመው ከምልዓተ-ለቀስተኛው የሚበዛው፣ በወንድም በሴትም፤ ሙስሊሙ ነው፡፡ እኔ በሆዴ በአግራሞት፤ “ሰውዬው ሙስሊም ናቸው እንዴ? እላለሁኝ፡፡ እኔ እስከማውቀው ድረስ ፊታውራሪ ክርስቲያን ናቸው! ምንድነው ጉዱ? ሙስሊም ሴቶች ወደቀብር እንደማይሄዱም አውቃለሁ፡፡ እንዴት እንዲህ እንደ አንድ ደግ መሪ የህዝብ አጀብ ደመቀላቸው?
ሥላሴ ቤተክርስቲያን አፋፍ ላይ ትልቅ መካነ-መቃብር ይታያል ብያለሁ፡፡ ግዙፍ ነው በጣም። ከመካከል የሀውልቱ ግድግዳ ላይ የፊታውራሪ በቀለ ኦጋቶ ፎቶ ይታያል፣ ከግርጌውም የህይወት ታሪካቸው ይነበባል፡፡
የፕሮግራም መሪው የህይወት ታሪካቸውን ያብራራው በተለይ ዶክተር ሙሉጌታ በቀለን አስከሬኑ እንዲገኝ ስላረጉት ጥረት በማመስገን ነበር። 
ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ ከአባታቸው ከግራዝማች ኦገቶ ጉቱና ከእናታቸው ከወይዘሮ ሻሹ ገልቹ በ1907 ዓ.ም በጢጆ አካባቢ በአሽበቃ ተወለዱ። ዕድሜአቸው ለትምህርት ሲደርስ መድረሳ ትምህርት ቤት ገብተው ቁርአን አክትመዋል። ከዚያም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነት ተቀብለው ለትምህርት ካላቸው ፍቅር የተነሳ ማንበብና መፃፍ ተምረዋል፡፡ ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ ባላቸው ትጋትና ሥራ ወዳድነት ተመርጠው በ1936 ዓ.ም ገና በወጣትነት ዕድሜአቸው ማለትም በ19 አመታቸው የመንግስት ሥራ በምስለኔነት በባብሌ ሜዳ ምክትል ወረዳ አስተዳዳሪነት ሥራ ጀምረዋል። እስከ 1939 ዓ.ም በምስለኔነት የሳጉሬ ምክትል ወረዳን አስተዳድረዋል፡፡
ከ1942 እስከ 1966 በአሰላ፣ አዳሚ ቱሉ፣ ጢዮ፣ በጭላሎ እና በጢቾ ከምስለኔነት እስከ አውራጃ ገዢነት ተሹመው አገልግለዋል! ከአቡነ ሉቃስና ከህዝቡ ጋር በመተባበር በ1959 ዓ.ም በከታር ወንዝ ሆፊ በሚባለው ቦታ የብረት ድልድይ አሰርተዋል። ከአሰላ እስከ በቆጂ ያለውን የመንገድ ሥራ ዋና አስተባባሪ ነበሩ፡፡ ከሳጉሬ ጢቾ በቦራ ለኩ በኩል የሚያልፈውን መንገድ ከደጃዝማች አባይ ካሳ በወቅቱ (የጢቾ አውራጃ ገዥ የነበሩ) ጋር ተባብረው አሰርተዋል፡፡
ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ በሸሬ ወረዳና በአዳሚ ቱሉ ወረዳ በሰሩባቸው ጊዜያት የአካባቢው ሕዝብ የሴቶች አለባበስ እንዲለወጥ አድርገዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ሴቶች እንደካባ የሚደርቡት ከከብቶች ቆዳ የተሰራና ቅቤ የተነከረ ኦምባ የሚባል ልብስ ነበር። ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ ይህንን ልማድ በጨርቅ አቡጀዲ እንዲለወጥና እንዲቀየር ጥረት አድርገዋል።
ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ ምንም ዓይነት የሃይማኖት ልዩነት ሳያደርጉ የአርሲ ሕዝብ ዘመናዊ ትምህርት እንዲማር በማድረግ ቀዳሚ ናቸው፡፡ ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ ዘመናዊ ትምህርት ምንም ዓይነት ክፍፍልና ልዩነት ሳይደረግ ለሕዝብ እንዲደረስና የተሳሳተ አመለካከቱን ሕዝቡ ቀስ በቀስ እንዲለውጥ ከግል ገንዘባቸው የቁርዓን አስተማሪ ቀጥረው በፈረቃ እንዲሰጥ አድርገዋል፡፡
ትምህርት ቤት ሲያሰሩ ከሚታወሱባቸው አባባሎች እንጨት ራሳቸው ይሸከሙ እንደነበረና፤ ይተዉ ሲባሉ “እኔ እንጨት ልሸከም፤ ተውሉኝ፣ አንተ ግን ልጅህን ለትምህርት ስጠኝ” ማለታቸው ነው፡፡
ፊታውራሪ በቀለ ኦገቶ በሃይማኖት መካከል ልዩነት የማያደርጉ ታላቅ ሰው ነበሩ፡፡ በሳጉሬ ከተማ ከግል መሬታቸው በመስጠት መስጊድ አሰርተዋል። እንዲሁም በሳጉሬ ከተማ የስላሴ ቤተክርስቲያንን አሰርተዋል፡፡”
አሃ! የዚህ ሁሉ ሙስሊምና ክርስቲያን ውህደት ምክንያት ለካ ይሄ ነው፤ አልኩ! ፊታውራሪ በቀለ፤ መስከረም 24 ቀን 1968 ዓ.ም. በግፈኛው የደርግ መንግሥት፣ የፍየል ወጠጤ ተዘፍኖባቸው፣ ከ16 ዘመዶቻቸውና ወዳጆቻቸው ጋር ተገድለዋል!! አስከሬናቸው በእንጨትና በጣውላ ርብራብ፣ ሬሳቸው ከነሙሉ ልብሳቸው በሚሥማር ተመቶ ተሰድሮ፤ ህዝብ እንዲያይ፣ ቀኑን ሙሉ በአደባባይ እንዲቆም ተደርጓል!

No comments: