Wednesday, November 18, 2015

ጠ/ሚ ኃይለማርያም የኮንሶን ውዝግብ ለማጣራት ቃል ገቡ

- በአካባቢው የሚታየው ውጥረት ግን ቀጥሏል፤


ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ሰገን አካባቢ ዞን የኮንሶ ወረዳ ሕዝብ ከመዋቅር ጥያቄ ማቅረብ ጋር በተያያዘ ደረሱብኝ ያሏቸውን ችግሮች ለማጣራት ቃል ገቡ።
የኮንሶ ሕዝብ በዞን ደረጃ ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄ በቅርቡ በይፋ ከማቅረቡ ጋር ተያይዞ የክልሉ መንግሥት ባሰማራው ልዩ ኃይል ወታደሮች እየተወሰዱ ያሉ ኢ-ሰብአዊ እርምጃዎችን በመቃወም ከአካባቢው ኅብረተሰብ የተውጣጡ የሀገር ሽማግሌዎችና በኅብረተሰቡ የተመረጡ የኮሚቴ አባላት ጥቅምት 29 ቀን 2008 ዓ.ም አቤቱታቸውን ለጠ/ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ አቅርበዋል።
ጠ/ሚኒስትሩም የኮንሶን ሕዝብ አቤቱታ በጽ/ቤታቸው ከተቀበሉ በኋላ ወዲያውኑ ከተወካዮቹ ጋር በስልክ የተነጋገሩ ሲሆን፤ በዚህም ንግግር አንድ ቡድን በማቋቋም ሁኔታው እንዲጣራ እንደሚያደርጉ ለተወካዮቹ አረጋግጠውላቸዋል።
ከኮንሶ ለአቤቱታ ወደ አዲስ አበባ የመጡት ተወካዮች ለጠ/ሚኒስትሩ በፃፉት ደብዳቤ፤ የኮንሶ ሕዝብ የመዋቅር ጥያቄ በሠላማዊ መንገድ አቅርቦ ምላሹን በጉጉት እየጠበቀ ባለበት በዚህ ሰዓት፣ ጥያቄውን በማቅረባቸው ብቻ የክልሉ ልዩ የወታደር ኃይል በማሰማራት ሰዎችን ወደ ማሰር፣ ማስፈራራት፣
ማሳደድ በመገባቱ ምክንያትም ሰዎች የዕለት ተዕለት ኑሮአቸውና እንቅስቃሴያቸው መታወኩን ጠቅሰዋል። እናም ጠ/ሚኒስትሩ ይህን የኃይል እርምጃ እንዲያስቆሙላቸው፣ አጥፊዎችም በሕግ እንዲጠየቁ፣ ሕዝቡም ያቀረበው የመዋቅር ጥያቄ በሕግና በሥርዓቱ መሠረት ምላሽ እንዲያገኝ በደብዳቤያቸው ጠይቀዋል።
የኮንሶ ሕዝብ ተወካዮች ከጠ/ሚኒስትሩ ጋር ተነጋግረው ምላሽ ካገኙ በኋላ ለሰንደቅ ጋዜጣ እንደተናገሩት በጠ/ሚኒስትሩ የተስፋ ቃል መደሰታቸውንና ችግሩንም ይፈቱልናል ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል።
የኮንሶ ሕዝብ በዞን እንድንዋቀር ይፈቀድልን የሚል ጥያቄ ካቀረቡ በኋላ ጉዳዩን ተከታትለው እንዲያስፈፅሙ ሕዝብ ከወከላቸው 12 ኮሚቴዎች መካከል ሦስት ያህሉን ጨምሮ በርካታ ሰዎች መታሰራቸው ታውቋል። እስከትናንት ከሰዓት በኋላ ድረስ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ቃል የገቡለት አጣሪ ቡድን ስለመቋቋሙ የታወቀ ነገር የሌለ ሲሆን፤ በኮንሶ አካባቢ ውጥረቱ እንዳለ ነው። በዚህም ምክንያት ት/ቤቶችን ጨምሮ መንግሥታዊ ተቋማት ማለትም የወረዳ ጽ/ቤት፣ የግብርና፣ የጤና፣ የትምህርት እና ሌሎች ተቋማት የዕለት ተዕለት ሥራቸውን ማከናወን የማይችሉበት ደረጃ ላይ መድረሳቸውን ከአካባቢው ያገኘነው መረጃ ጠቁሟል።

source

- Sendek NewsPaper

No comments: