Monday, April 1, 2013

በምንበላው ሲገርመን በምንተነፍሰው?

እነሆ ዛሬ ደግሞ ከመገናኛ ወደ ገርጂ ልንሳፈር ነው። ፀሐይን ሰሞነኛው ደመና ሸፍኗታል። ልክ አንዳንዱን እውነታ ሰሞነኛ ማስተባበያ እንደሸፈነው።
ኑሮ፣ ኑሮ ሰውን ወዝውዞ ወዝውዞ የሆነ የሕይወት ቱቦ ውስጥ ጥሎ የረሳው ይመሳለል። መንገዱ ላይ ቆሜ በትርምሱና በጫጫታው መሀል የማሰላስለው ከአድማስ ወዲህ ማዶ ስላለው ስለእኛ ስለሰው ልጆች ትግል ነው። ሁሉም ነገር በትግል ሲባጎ ተጠፍንጎ የተሳሰረ ሆኖ ይታየኛል።

ሁሉን የሚችለው ብርቱው የሰው ልጅ በአልበገር ባይነት ፅናትና መንፈስ ለመኖር ግብግብ እንደገጠመ አየዋለሁ። ቁልቁል ወደቤቷ የምትሰደደው ጀንበር የምትነግረኝ ግን ሌላ ነው። የሽንፈት ደመና የመከራ ዝናብ ቋጥሮ እኛ ላይ የሚለቀው አስመስላ ታሳየናለች። ለታክሲ ሠልፍ የያዘው መንገደኛም ገልመጥ እያለ በጠቋቆረው  ደመና ውስጥ አንድ ነገር ፈልጎ ያጣ ይመስላል። ‹‹ይህ ነው የእኛ ሕይወት?›› ትላለች አንዲት ቀጭን ጠይም ረዢም ወጣት። ያለ ዕድሜዋ የተሸበሸበ ቆዳዋን ስመለከት ብዙ ያልተኖሩ ልጅነቶች ይታወሱኝ ጀመር። ‹‹አይ እናት አገሬ! ስንቱን ያለ ዕድሜው አገረጀፍሽው?›› ይላል ሳላየው ልጁቱን እንደ እኔው ሲያስተውላት የቆየ ጎልማሳ። ‹‹የቱ ነው የእኛ ሕይወት ማለት?›› ትላታለች ግራ የተጋባች ጓደኛዋ። ‹‹ያ ሩቅ ያለው ደማና ነዋ! ከደመናው ጀርባ ፀሐይ እንዳለች እርግጠኛ የሆንበት ደመና።


 የእኛም ሕይወት እንደዚህ አይደል? ከችግሮች በስተጀርባ ዘላቂ መፍትሔዎች እንዳሉ እናውቃለን። ግን ከደመናው ጋር ፍቅር ይዞን ነው መሰል ወይም ሌላ ይሁን ብቻ አላውቅም ይኼው በየሄድንበት ሠልፉና መጉላላቱ… ኧረ ተይኝ፤›› ብላት በረጂሙ ተነፈሰች። ‹‹ለዳቦ፣ ለቢል ክፍያ፣ ለታክሲ፣ ለአውቶቡስ፣ ወዘተ እንሠለፋለን፡፡ አቤቱታ ለማቅረብ ግን ሠልፍ አይፈቀድልንም፤›› ስትል እኔና ጎልማሳው ተያየን። የገመትነው እውነት የልጅቷ ልጅነት ውስጥ ነበር። አቤት! መንገድ ሲያገናኝ ስንት እውነት ይታያል?

ወዲያው አንድ የገርጂ ታክሲ መጣ። የምንሞላው ሰዎች ብቻ ገብተን ቦታ ቦታችንን ስንይዝ ቀሪው ሠልፈኛ ተስፋ በመቁረጥ ስሜት ተረብሾ ይቁነጠነጥ ነበር። ‹‹እኔምለው ከመቼ ወዲህ ነው አዲስ አበባ እንዲህ ሰው የበዛው?›› ይላል አንድ ‹‹ዳያስፖራ›› መሰል ተሳፋሪ፡፡ ‹‹አልሰሜን ግባ በለው አሉ! መንግሥት አልሰማን አለ ብለን የምንጮኸው ዝም ብለን ነው፡፡ መጀመሪያ መቼ እርስ በእርሳችን ችግራችንን አወቅነው ሲባል ማን ሰምቶ? ግን ይኼው፤›› ብላ አንዲት ነገር ነገር የሚላት ሴት አጠገቡ እንደተቀመጠች ተንበለበለች።

‹‹ይቅርታ! እኔ እኮ እዚህ አገር ስለማልኖር ነው የጠየቅኩት?›› ሲላት፣ ‹‹ጭራሽ እናንተ አይደላችሁ እንዴ እኛ እናውቅላችኋለን እያላችሁ በየኢንተርኔቱ ጓዳ ስለአገሬና ስለሕዝቧ የምትወሸክቱት? እኔምለው ለመሆኑ በአሁኑ የአዲስ አበባ  ምርጫ ልትሳተፉ አስባችኋል?›› ስትለው ደንግጦና ግራ ገብቶት ሁሉንም ተሳፋሪ ይቃኝ ጀመር። እኛም እንደሱ ደንግጠን መተያየት ጀመርን፡፡ ብዙም ሳይቆይ እየተንቀሳቀ የነበረውን ታክሲ አስቁሞ፣ ‹‹እባክህ ቦታ ቀይረኝ?›› አለ ወያላውን። ሊወርድ አስቦ የሠልፉ ነገር ሐሳቡን እንዳስቀየረው ያስታውቅበታል። አንድ ፈቃደኛ ተሳፋሪ ከኋላ መቀመጫ ተነስቶ ከቀየረው በኋላ ጉዟችን ቀጠለ። ‹‹አይ ታክሲ ስንቱን ያሳየናል?›› ይላል ከሾፌሩ ጀርባ ያለ ጎልማሳ። ሕይወት በውስብስብ ገጽታዋ ብዙ እያሳየችን የኖርነው ቢያንስ ግማሹ ታክሲ ውስጥ መሆን አለበት።

ቀለበት መንገዱን ይዘን መምዘግዘግ እንደጀመርን፣ ‹‹ይኼ ቀለበት መንገድ የስንቱን ቀለበት አስወለቀ?›› አለ የማይናገር የሚመስለው ወያላ መንገዱ መሀል እየዘለለ የሚሻገር ትልቅ ሰው እያየ። ‹‹እንዴት?›› ሲሉት፣ ‹‹ድልድይ ፈልጎ መሻገር አላስችል ብሎት ስንቱ ነው ያለቀው?›› ከማለቱ በቅጡ ያላስተዋልናቸው አዛውንት፣ ‹‹ጊዜ ጠብቀህ ተናገር ውኃ ሲጎድል ተሻገር ነዋ ከጥንትም ብሂሉ የዘንድሮ ሰው ምክር ጠላ እንጂ?›› ብለው እጃቸውን አመናጨቁ፡፡ መጥኔ ማለታቸው ነው።

 የደመናው ገጽታ ከጨለማው በፊት ሌላ ዓይነት ጨለማ የፈጠረ ይመስላል። ወያላው ሒሳብ መቀበል ጀምሯል። በውል ፊቱን ማየት ያልቻልነው ተሳፋሪ መስኮት ከፍቶ አይዘጋም በማለት ጭቅጭቅ ብጤ ለመጀመር ዳር ዳር ይላል። ጭቅጭቁ ብዙ ሳይገፋ አንድ ስልክ ጮኸ። ስልኩን ያነሳው ወጣት ተሳፋሪ፣ ‹‹መጣሁ! መጣሁ! ሜክሲኮ ደርሻለሁ። እውነት! እውነት!›› ብሎ  ይዋሻል። አባባሉ ጆሯችንን ሰቅጥጦታል። ይባስ ብሎ ነው መሰል ስልኳ ሲጮህ ሳንሰማው መነጋገር የጀመረችው ሌላ ወጣት ሴት ‹‹አሁን … እ …  ወደ ሲኤምሲ እየደረስኩ ነው፤›› ትላለች። አዛውንቱ በጩኸት፣ ‹‹ኧረ ሾፌር መኪናውን አቁምልኝ፤›› ካሉ በኋላ ወያላውን ይወርዱበት ጀመር። ‹‹ምን ነው አባት ምን አጠፋሁ?›› ሲላቸው ‹‹ሞላጫ! ዋሽተኸኝ ለምን ገርጂ ነው የምሄደው ብለህ ጫንከኝ?›› ብለው አንባረቁበት። ወያላው ነገሩ ወዲያው ገባውና፣ ‹‹አሁን ስልክ ሲነጋገሩ የሰሟቸው ሰዎች የቀጠሩትን ሰው ስላረፈዱበት የተናገሩት ውሸት ነው እንጂ የምሄደው ገርጂ ነው፤›› ብሎ አረጋጋቸው።

ከተሳፋሪዎች መካከል አንዳንዶቹ ሆዳቸውን ይዘው ሲስቁ አንዳንዱ እያዘነ፣ ‹‹ሞባይል ከመጣ ዘመን ቅጡን ይጣ!›› ይባባላል። ወዲያው የአዛውንቱ ስልክ ሲያቃጭል አነሱት። ‹‹የት ደርሰዋል?›› ተብለው ነው መሰል ‹‹ኧረ እኔም አላወቅኩት፣ አንዱ በሜክሲኮ ይላል ሌላዋ ሲኤምሲ እያለች ግራ ገብቶኛል፤›› ሲሉ የተሳፋሪዎች ሳቅ አጀባቸው። በምሬት መሀል ሳቅ ሲደባለቅ ዘና ያደርጋል፡፡

ጉዟችን እንደቀጠለ ነው። ኢምፔሪያል አካባቢ ሁለት ወራጆች ወርደው አራት ተሳፋሪዎች በምትካቸው ተጫኑ። ሾፌሩ በመስኮቱ አሻግሮ በተቃራኒ አቅጣጫ የሚመጣ ባለታክሲ ወዳጁን በመጣበት መንገድ ትራፊክ ፖሊስ መኖር አለመኖሩን ይጠይቀዋል። ያኛውም፣ ‹‹የለም!›› ብሎ ይመልሳል። ‹‹ጫን በደንብ!›› ይለዋል ሾፌሩ ወያላውን፡፡ እኛ ደግሞ ዝም። ‹‹ለማን አቤት ይባላል? ቢባልስ እስካሁን ያልነው አይበቃም ነበር?›› ይላል ጎልማሳው። ጠይሟ ቆንጆ ወጣት በበኩሏ፣ ‹‹አስተዳዳሪዎቻችን እንኳን ተነግሯቸው ላያቸው ላይ አስተዳደር ቢገነባባቸውም አይነቁ፤›› ትላለች የሚስቅ ይስቃል። ‹‹ተስፋ መቁረጥ የለም!›› ብሎ አንድ ድምፅ ሲጮህ ሁላችንም ዞረን አየነው። ሙሉ ልብስ ነው የለበሰው። በእጁ የ‹‹ላፕቶፕ›› ቦርሳ ይዟል።

‹‹እኔን ከመረጣችሁኝ ችግራችሁን ሁሉ ገደል ነው የምሰደው፤›› ብሎ ቅስቀሳውን ጀመረ። ወዲያው ዕጩ የግል ተወዳዳሪ መሆኑን ነገረን። ‹‹ለመሆኑ …›› አለው አንድ ተሳፋሪ አጠገቡ ቁጭ እንዳለ። ‹‹… እንዴት ብለህ ነው የታክሲ ሠልፍንና እጥረትን እስከነአካቴው ልታስወግድ የምትችለው?›› ብሎ ጠየቀው። ሙሉ ፈገግታ ፊቱን ወርሶት ‹‹ይኼማ ቀላል ነው። አያችሁ ብዙዎቻችን ከእንቅስቃሴ ጋር ተቆራርጠናል። ጠንካራና ጤናማ ዜጋ ለአንድ አገር ህልውና ወሳኝ ነው። ጠንካራና ጤነኛ ኅብረተሰብ የአገሩን ዳር ድንበር  ከማስከበር አልፎ በጥሩ ሁኔታ ሳይደክመው እየሠራ ጥሩ ግብር ከፋይ ይሆናል። ስለዚህ የታክሲ ችግርን መቅረፍ የሚቻለው በእግር ለመሄድ ስንወስን ነው። ጤናችሁንና ገንዘባችሁን ገና በብዙ ጉዳዮች ዙሪያ ስለማተርፍላችሁ ግድ የለም እኔን ምረጡ! አመሰግናለሁ፤›› ሲል ታክሲዋ ደም በለበሱ ዓይኖችና ንዴት በሚያቁነጠንጣቸው ተሳፋሪዎች ተሞላች። ‹‹አይ ምርጫና አልጫ!›› የሚሉት አዛውንቱ ነበሩ።  

ወደ መዳረሻችን እየተቃረብን ነው። ወያላው ኮርያ ሆስፒታል አካባቢ የጫነውን ተሳፋሪ ሒሳብ ሲቀበለው ተሳፋሪው፣ ‹‹ለመሆኑ መቼ ነው እናንተም የካሽ ሬጅስተር ማሽን የምታስገቡት?›› በማለት ጠየቀው። ወያላው እየሳቀ፣ ‹‹እንግዲህ መመርያው ወጥቶ ሲፀድቅ ነዋ። መቼም እዚህ አገር ሁሉ ነገር ላይ የአፈጻጸም ችግር ሲኖር ‹‹ቫት›› ላይ ቀልድ የሚባል ነገር የለም። ምናለበት ሌላውም ነገር ላይ ቀልድ አላውቅ ብንል?›› ብሎ ይመልስለታል። ‹‹አዲስ ንጉሥ እንጂ ለውጥ መቼ መጣ? ብሎ ጨርሶታል እኮ!›› ይላል ሌላው ከኋላ። ‹‹አሁንስ የሰለቸን የኋላቀር ርዝራዦችን ትንታኔ መስማት ነው፤›› ይላል ከጎኑ የተቀመጠ ጎልማሳ። ሁሉም ተሳፋሪ የጎሪጥ መተያየት ጀመረ። ውይይቱ በሁለት ጎራ ተከፍሎ አረፈው።

‹‹በለው! እውነተኛው የምርጫ ክርክርስ ይኼ ነው፤›› ይላል አንድ ቀልቀል የሚል ልጅ እግር። ከአንደኛው ወገን በቀልድ መልክ አንዱ እንዲህ ይላል፡፡ ‹‹ይገርማችኋል ከማጣቴ የተነሳ አንድ ሰሞን የማውቀውን ሰው ሁሉ ተበድሬ ተበድሬ የቀረኝ ራሱን ኑሮን መበደር ሆነ። በኋላ ኑሮ ዘንድ ሄጄ ኑሮ ሆይ! እባክህ ሲኖረኝ ልክፈልህ አሁን ልበደርህና ልኑርበት አልኩና ‹አድቫንስ› ጠየኩት። እንዲህ የሚባል ነገር የለም! እያለህ ካልሆነ ከሌለህ የለህም! ብሎ አውጇል አለኝ። እኔም አውጇል ባለው ፈንታ ዘፍኗል ይለኛል ብዬ ጠብቄ ኖሮ ማን ነው ያወጀው ስለው፣  ‹አብዮታዊው መንግሥትህ  ነዋ!› አይለኝ መሰላችሁ? እውነቴን እኮ ነው እያለ አጠገቡ ያሉ ሰዎችን እጅ ይመታል። መሀላና ቀልድ እውነትና ውሸት የተሰባጠሩበት ዘመን፡፡

 ‹‹እውነቱን እኮ ነው! ባይሆን ኑሮማ ሙስና እንዲህ ሥር ይሰድ ነበር?›› ትላለች ከፊት አካባቢ የተቀመጠችው ወጣት። ‹‹የዘንድሮ ሰው ምሥጋና የለሽና ራስ ወዳድ ብቻ ነው። በማን ላይ ሆነሽ ማንን ታሚያለሽ አሉ፡፡ እንዲህም የልብን መናገር ያስቻላችሁ ጀግናው ኢሕአዴግ ነው፤›› ብሎ አንዱ ሲመልስ ከዚያኛው ወገን ሦስት የሚሆኑ ተሳፋሪዎች በሳቅ ታክሲዋን አናጉዋት። ሳቁ ያልገባን ግራ ተጋብተን ስናያቸው፣ ‹‹አይ! አይ! ዲሞክራሲ ግራዚያኒን የሚያህል ጨፍጫፊ ለምን በስሙ መናፈሻ ተሠራለት ብለን በተሰበሰብን አይደል እንዴ የታፈስነው? አይ አገር! አይ ዲሞክራሲ! ‘እማማ ኢትዮጵያ ሞኝ ነሽ ተላላ፣ የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ!’ ማለትስ ዛሬ ነው፤›› ሲል አንደኛው ባለተራው ተቀብሎ ‹‹ታያላችሁ ኢቲቪ ሰሞኑን ‘ለሽብር ሲሰባሰቡ የተገኙ’ ብሎ ዶክመንተሪ ሲሠራብን ይላል። ወያላው ታክሲው ሲቆምለት ሁኔታው ቀፎት ስለቆየ ነው መሰለኝ በተጣደፈ ድምፅ ‹‹መጨረሻ!›› አለ፡፡ ልንወርድ ስንጋፋ አንዱ፣ ‹‹በምንበላው ሲገርመን በምንተነፍሰው ጭምር ቫት ይምጣ? የምሥራች! ዲሞክራሲ ቫት ተጣለባት!›› ሲል አዛውንቱ ቀበል አድርገው ‹‹የእስራት ነው የገንዘብ?›› ብለው በጥያቄ የጉዟችንን ጭውውት ቋጩት፡፡ መልካም ጉዞ!   

No comments: