Wednesday, March 13, 2013

በአፄ ዮሃንስ 4ኛ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን የትግርኛ መጽሐፍ ተመረቀ

በአፄ ዮሃንስ 4ኛ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን የትግርኛ መጽሐፍ ተመረቀ

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 3/2005(ዋኢማ) - “እምቢታ አንፃር ወረርቲ” በሚል ርዕስ በትግርኛ ቋንቋ የተዘጋጀ የአፄ ዮሃንስን የህይወት ታሪክ የሚዳስስ መጽሐፍ ተመረቀ።

በመምህር ገብረኪዳን ደስታ የተጻፈው መፅሀፍ 534 ገጽ ሲኖረው እስካሁን በታሪክ መሀፍት ያልተዳሰሱትንና የአጼ ዮሃንስ ተግባራትን የሚያሳዩ ታሪኮችን በውስጡ ማካተቱን በመጽሐፉ ምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ወቅት ተገልጿል።

የመጽሐፉ ደራሲ መምህር ገብረኪዳን ደስታ እሁድ ዕለት የተለያዩ እንግዶች በተገኙበት በአክሱም ሆቴል መፅሀፉ በተመረቀበት ወቅት እንደተናገሩት፤ እውነተኛው የአፄ ዮሃንስ ታሪክ እስካሁን ድረስ ተጽፏል ብለው እንደማያምኑ በመጥቀስ የአፄ-ዮሃንስ ትክክለኛ ማንነት ግን አገራቸውን ከየትኛውም ጠላት ለማዳን እስከ መጨረሻው የደም ጠብታ ድረስ የታገሉ ሰማዕት እንደሆነ ገልጸዋል።

ወጣቱ ትውልድ ሃቅን ተከትሎ ታሪክን መዘከር እንዳለበት የመከሩት ጸሃፊው ታሪክ የሚጻፈው  እንዱን ለማስከፋትና ሌላውን ለማስደሰት እንዳልሆነና ወጣቱ ትውልድ የታሪክ መሀፍትን  እራሱ ተመራምሮ እውነታውን እንዲያውቅ ነው ብለዋል።

በመጽሐፍ ምረቃው ላይ በክብር እንግዳነት የተገኙት ክቡር ልዑል ራስ መንገሻ ስዩም ባደረጉት ንግግር መጽሓፉ ለምረቃ በመብቃቱ በጣም ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸው፤  መጽሐፉ የኢትዮጵያን ህዝብ ታሪክና ባህልን ለመጪው ትውልድ በማስተላለፍ ረገድ ወሳኝ ሚና እንዳለው ተናግረዋል።

No comments: