Wednesday, March 13, 2013

ኡሁሩ ኬንያታ አራተኛው የኬንያ ፕሬዝዳንት ሆነው ተመረጡ

አዲሰ አበባ፤ መጋቢት 2/2005 (ዋኢማ) - በኬንያ በተካሄደው ፕሬዝዳንታዊ የምርጫ ውድድር ኡሁሩ ሙይጋይ ኬንያታ አሸናፊ መሆናቸውን የአገሪቱ ገለልተኛ የምርጫና የወሰኖች ኮሚሽን አስታወቀ፡፡

ኮሚሽኑ ትናንት ይፋ ባደረገው የምርጫ ውጤት መሰረት ኡሁሩ ኬንያታ 50 ነጥብ 03 በመቶ በሆነ ድምጽ በማሸነፍ የኬንያ አራተኛው ፕሬዝዳንት መሆን ችለዋል፡፡ የቀድሞ የኬንያ ፕሬዝዳንት የነበሩት የጆሞ ኬንያ ልጅ የሆኑት ኡሁሩ ኬንያታ 51 ዓመት ዕድሜ ያላቸው ሲሆን ከቀደሙት የኬንያ ፕሬዝዳንቶች ሁሉ በዕድሜ ያነሱ መሆናቸውን ዘገባዎች አመልክተዋል፡፡

ተመራጩ ፕሬዝዳንት ውጤቱ ይፋ ከሆነ በኋላ ባደረጉት ንግግር "ዛሬ የዴሞክራሲ፣ የሠላምና የሕዝብ አሸናፊነትን እናከብራለን፤ በምርጫው ከግምት ውጭ በሆነ መልኩ የፖለቲካ ብስለታችንን ለዓለም አሳይተናል" ብለዋል፡፡

ተቀናቃኛቸው በምረጡኝ ዘመቻው ያሳዩትን ብርቱ ፉክክር በማድነቅ አገሪቱን ወደፊት ለማራመድ በሚደረገው ጥረት በጋራ መሥራት እንደሚፈልጉም ግልጽ አድርገዋል፡፡ በውድድሩ ተቀናቃኛቸው የነበሩት ጠቅላይ ሚኒስትር ራይላ ኦዲንጋ 43 ነጥብ 8 በሆነ ድምጽ መሸናፋቸውን ኮሚሽኑ ቢያሳውቅም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግን በምርጫው ውጤት እንደማይስማሙ ገልጸዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ራይላ ኦዲንጋ ምርጫው የተጭበረበረ በመሆኑ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንዲያመራ እንደሚፈልጉ ዘገባዎች አመልክተዋል፡፡ ኡሁሩ ኬንያታ የኬንያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሆነው በማገልገል ላይ የነበሩ ሲሆነ እንደ አውሮፓውያን አጣጠር በ2007 የተካሄደውን ብሔራዊ ምርጫን ተከትሎ በተፈጠር ብጥብጥ ሄግ የሚገኘው ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት በዘር ማጥፋት ወንጀል ተጠያቂ አድርጓቸዋል፡፡

ይህን ተከትሎ ኡሁሩ ኬንያታ በምርጫው ማሸነፍ አሜሪካን ጨምሮ ምዕራባውያን ሀገራት ከኬንያ ጋር ያላቸው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ስጋት እንደተደቀነበት ተንታኞች ያስረዳሉ፡፡ በኬንያ የተካሄደው የምርጫ ሂደት ግልጽነት የተሞላበት እንደነበር አብዛኞቹ ኬንያውያን እየገለጹ ናቸው፡፡ ምርጫውን በቅርበት ሲታዘቡ ከነበሩ ዓለም አቀፍ ታዛቢዎች መካከል ለሮይተርስ እንደገለጹት "ምርጫው ተአማኒነት የጎደለው ነበር ለማለት የሚያስደፍር አንዳችም ነገር የለም"፡፡

እንደ ኢዜአ ዘገባ ራይላ ኦዲንጋ እንደ አውሮፓውያን አጣጠር በ2007 በተካሄደው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ውጤቱ ተጭበርብሯል በሚል ተቃውሞ ያሰሙ ሲሆን የአገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤትም እምነት የማይጣለበት በመሆኑ ጉዳዩን ወደ ሕግ አላቀርብም ማለታቸውን ተከትሎ ከፍተኛ ብጥብጥ በአገሪቱ መከሰቱ ዴይሊ ኔሽንና ሮይተርስን ዋቢ አድርጎ ኢዜአ ዘግቧል፡፡

No comments: