Thursday, March 14, 2013

ትክክለኛ አስተሳሰብ ሲኖርህ ትክክለኛ ሰው ትሆናለህ

ለቃላት ትክክለኛና ጥርት ያለ ትርጉም ለመስጠት ብሎም የቃላትን ብዥታና (vagueness) አሻሚነትን (ambiguity) ለማስወገድ ለእያንዳንዱ ቃል በተለያየ አውድ ውስጥ የሚኖረውን ብያኔ በትክክል መረዳትና እያንዳንዱንም ቃል በተገቢውና በትክክለኛ ቦታ ብቻ መጠቀም እንደሚገባ የቋንቋ ፍልስፍና ሊቃውንት ያስተምራሉ፡፡ ለምሳሌ “ደረቅ እንጀራ አለ” እና “ለምለም እንጀራ አለ” የሚሉትን በአዲስ አበባ እና በሐዋሳ ከተሞች የተለመዱ ሁለት የእንጀራ ሽያጭ ማስታወቂዎችን የቃላት አጠቃቀም ትክክለኝነትን ብናነጻጽር “ደረቅ እንጀራ” የሚለው ቃል “ድርቆሽ እንጀራ” የሚለውንም ትርጉም በውስጡ ስለሚይዝ የበለጠ አሻሚ (ambigious) ሆኖ እናገኘዋለን፡፡
የእስራኤሉ ንጉስ ዳዊት የሚሞትበት ቀን በቀረበ ጊዜ ልጁ ሰሎሞንን ያዘዘው ዋነኛ ትእዛዝ “ሰው ሁን” የሚል እንደነበር በመጽሐፈ ነገስት ቀዳማዊ እናነባለን፡፡ ሰው ሆኖ ከተፈጠረ በኋላ ሰው ሁን ተብሎ መታዘዙ ሰው መሆን በስጋና በደም ጸንቶ ከመንቀሳቀስ የዘለለ መለኪያ እንዳለው የሚያስረዳ ነው፡፡ ታላቁ የግሪክ ፈላስፋ አሪስጣጣሊስ “ማሰብ የሰውነት መገለጫ ነው” ሲል ደግሞ አንዱ መስፈሪያ ማሰብ (thinking) መሆኑን ይመሰክራል፡፡ “ማሰብ የሰውነት መገለጫ ነው” በሚለው ዓረፍተ ነገር የተስማማ ሰው “ትክክለኛ አስተሳሰብ ያለው ሰው ደግሞ ትክክለኛ ሰው ነው” የሚለውን ዓረፍተ ነገር እውነትነትም በአመክንዮ መርህ መቀበል ይኖርበታል፡፡ በርግጥም ሁሉም ሰዎች ማሰባቸው እውነታ ቢሆንም ሁሉም ሰዎች በትክክል ማሰባቸው ግን በጥያቄ ምልክት መቀመጥ የሚገባው ጉዳይ ነው፤ ምክንያቱም በህጸጽ የተሞላ አስተሳሰብ ያላቸው በርካታ ሰዎች ህጸጾቻቸውንና የተሳሳተ ድምዳሜያቸውን በየደቂቃው በንግግራቸውም ሆነ በጽሁፋቸው ሲገልጹ ይስተዋላሉና፡፡ ለመሆኑ ትክክለኛ አስተሳሰብ ምንድን ነው?
ትክክለኛ አስተሳሰብ (correct thinking) በአመክንዮ ላይ ተመስርቶ ድምዳሜ የሚሰጥበት የአስተሳሰብ ስልት ነው፡፡ በእንግሊዝኛው (Logic) የሚል ስያሜ የተሰጠው ይህ ሃሳብ ሎጎስ (logos) ከሚለው የግሪክ ቃል የመጣ ሲሆን የትክክለኛ አስተሳሰብ ጥበብ የሚል ትርጉም ያዘለ ነው፡፡
ትክክለኛ አስተሳሰብ የሚከተለው የራሱ የሆነ ቀመር አለው፡፡ የመጀመሪያው መሰረታዊ የትክክለኛ አስተሳሰብ ቀመር ማሳመኛ አንቀጽ (argumnet) ይባላል፡፡ አንድ ማሳመኛ አንቀጽ እርስ በርሳቸው የተሳሰሩ አንድ ወይም ከአንድ በላይ እውነት ወይም ሀሰት ሊባሉ የሚችሉ ዓረፍተ ነገሮችን ወይም ማስረጃዎችን (premises)፤ እንዲሁም ከእነዚህ ማስረጃዎች የመነጨ አንድ መደምደሚያ ዓረፍተ ነገር (conclusion) ሊኖረው ይገባል፡፡
ትክክለኛ የአስተሳሰብ ቀመር ማንኛውንም ፍልስፍና ለመረዳትም ሆነ ለመስራት የምንገለገልበት የፍልስፍና ቋንቋ ነው፡፡ በዚህ ቀመር የሚመነጨው ድምዳሜ ፍጹማዊ (deductive) ወይም ምናልባታዊ (inductive) መልክ ሊኖረው ይችላል፡፡
ፍጹማዊ የሚባለው ቀመር የማሳመኛ አንቀጹ ድምዳሜ ከቀረበው ማስረጃ በፍጹም እርግጠኝነት (certainity) የመነጨ ሲሆን ነው፡፡ ይህም አንድ ሰው ባቀረበው ማሳመኛ ውስጥ የዘረዘራቸው ማስረጃዎች በሙሉ እውነት ከሆኑ ከዚህ የመነጨው ድምዳሜ በምንም መንገድ ሀሰት ሊሆን አይችልም፡፡ በሂሳብ ስሌት፣ በብያኔ ወይም በሲሎጂዝም ላይ ተመስርቶ የሚሰጡ ድምዳሜዎች የፍጹማዊ ድምዳሜ ማሳያዎች ናቸው፡፡ ለምሳሌ “ኢትዮጵያውን በሙሉ ብርቱ የሀገር ፍቅር ስሜት አላቸው”፤ እና “አቶ ኦንጋዬ ኢትዮጵያዊ ናቸው”፤ የሚሉት ሁለት የማስረጃ ዓረፍተ ነገሮች “እውነት” መሆናቸውን ካረጋገጥንና ከዚህም “አቶ ኦንጋዬ ብርቱ የሀገር ፍቅር ስሜት አላቸው” የሚል መደምደሚያ ላይ ብንደርስ በመደምደሚያ ስለቀረበው ዓረፍተ ነገር እውነትነት መናገር ያለብን በፍጹም እርግጠኝነት እንጂ በምናልባት አይደለም ማለት ነው፡፡
በሌላ በኩል በማሳመኛ አንቀጹ መደምደሚያ ላይ የተቀመጠው ዓረፍተ ነገር ከቀረቡት ማስረጃዎች በምናልባት (probability) የመነጨ ማሳመኛ ምናልባታዊ (Inductive) ቀመር ተከትሏል ይባላል፡፡
ይህም ማለት በማሳመኛው አንቀጽ ውስጥ በማስረጃነት የቀረቡት ዓረፍተ ነገሮች በሙሉ እውነት መሆናቸውን ብናረጋግጥ እንኳን ከማስረጃዎቹ የመነጨው መደምደሚያ እውነት ወይም ሀሰት የመሆኑ ጉዳይ በምናልባት ላይ የተመሰረተ ነው፡፡
በትንበያ፣ በምስስሎሽ፣ በምልክት፣ እንዲሁም በምክንያትና በውጤት ትስስር ላይ ተመስርተው የሚቀርቡ ማሳመኛዎች የምናልባታዊ አስተሳሰብ ቀመርን መርህ የተከተሉ ናቸው፡፡ ለምሳሌ “አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ አስር ክፍለ ከተማዎች ይገኛሉ፡፡” እና “በየካ፣ በቦሌ ፣በጉለሌ፣ በኮልፌ ቀራንዮና በአቃቂ-ቃሊቲ ክፍለ ከተማዎች ውስጥ ተፈጥሯዊ የመናፈሻ ስፍራዎች (Parks) ይገኛሉ” የሚሉት በማስረጃነት የቀረቡ ዓረፍተ ነገሮች እውነት እንደሆኑ ካረጋገጥንና ከዚህም ተነስተን “በተቀሩት አምስት ክፍለ ከተማዎች ውስጥም እንዲሁ ተፈጥሯዊ የመናፈሻ ስፍራዎች (Parks) ይገኛሉ” የሚል መደምደሚያ ላይ ብንደርስ በመደምደሚያ ስለቀረበው ዓረፍተ ነገር እውነትነት መናገር ያለብን በምናልባት እንጂ በፍጹም እርግጠኝነት አይደለም ማለት ነው፤ ምክንያቱም ስለቀሩት አምስት ክፍለ ከተማዎች ይዞታ በማሳመኛ አንቀጹ የቀረበ ግልጽ ማስረጃ ስለሌለና ድምዳሜውን የምናመነጨው በይሆናል ስለሆነ ነው፡፡
ከህጸጽ የጸዳና ትክክለኛ አስተሳሰብ ያለው ሰው ጥርት አድርጎ የማሰብ አቅም ይኖረዋል፡፡ ጥርት አድርጎ የሚያስብ ሰው ደግሞ ጥርት ያለና ትክክለኛ ቋንቋ ይናገራል፡፡ ትክክለኛ ቋንቋና ትክክለኛ አስተሳሰብ የተቆራኙ ናቸው፡፡ ማለትም ፍልስፍና ያለ ቋንቋ ሊገለጽ አይችልም፤ ቋንቋም በፍልስፍና ካልተቃኘ ጥርት ያለና ትክክለኛ ሊሆን አይችልም፡፡
ትክክለኛ አስተሳሰብ ሊመጣ የሚችለው በማንኛውም ቋንቋ ውስጥ የሚገኙ ቃላትን ትክክለኛ ፍቺና ብያኔ አውቆ በተገቢው ቦታ ላይ ብቻ መጠቀም ሲቻል ነው፡፡ ቀደምት የግሪክ ፈላስፎች ፍልስፍናቸውን የጀመሩትም በዚሁ የቃላት ፍቺ ነበር፡፡ ለምሳሌ የአፍላጦን መምህር ሶቅራጥስ (dialectic) ተብሎ በሚታወቀው የፍልስፍና ዘዴው በጥያቄና መልስ ከበርካታ ሰዎች ጋር በሚያደርገው ምልልስ የሥነ-ምግባር ጽንሰ ሃሳቦችን ትክክለኛ ብያኔና ምንነት ጥርት አድርጎ ለማወቅና ለማሳወቅ ከፍተኛ ትግል ያደርግ እንደነበር ከምዕራባውያን የፍልስፍና ታሪክ እንማራለን፡፡ ሶቅራጥስ ተማሪዎቹ ፍትህ፣ ፍቅር፣ ጀግንነት፣ ትዕግስት የመሳሰሉት የስነምግባር ቃላት ትርጉም በራሳቸው ተመራምረው እንዲደርሱበት በነበረው ከፍተኛ ፍላጎት አንጻር የቃላቱ ፍቺ ነው ብለው የሚሰነዝሩትን ምላሽ ጎዶሎነት ወይም ስህተት በአመክንዮ ያሳያቸውና የተሻለና የመጨረሻውን ትክክለኛ ብያኔ እንዲፈልጉ ያበረታታቸው ነበር፡፡
ከዚህም ባሻገር የጥያቄና መልስ ተሳታፊዎቹ የሶቅራጥስን ተቋቁሞ (defense) መከላከል ሲያቅታቸውና ለቀረበው ቃል አንድ የተለመደ ፍቺ እንዲነግራቸው ሲጠይቁት በማህበረሰብ አስተሳሰብ (communal thinking) ላይ ጥገኛ እንዳይሆኑና በግል ፍልስፍና (individual thinking) መኖርን እንዲማሩ “የማውቀው አለማወቄን ብቻ ነው” የሚል መልስ ይሰጣቸው ነበር፡፡
ለቃላት ትክክለኛና ጥርት ያለ ትርጉም ለመስጠት ብሎም የቃላትን ብዥታና (vagueness) አሻሚነትን (ambiguity) ለማስወገድ ለእያንዳንዱ ቃል በተለያየ አውድ ውስጥ የሚኖረውን ብያኔ በትክክል መረዳትና እያንዳንዱንም ቃል በተገቢውና በትክክለኛ ቦታ ብቻ መጠቀም እንደሚገባ የቋንቋ ፍልስፍና ሊቃውንት ያስተምራሉ፡፡ ለምሳሌ “ደረቅ እንጀራ አለ” እና “ለምለም እንጀራ አለ” የሚሉትን በአዲስ አበባ እና በሐዋሳ ከተሞች የተለመዱ ሁለት የእንጀራ ሽያጭ ማስታወቂዎችን የቃላት አጠቃቀም ትክክለኝነትን ብናነጻጽር “ደረቅ እንጀራ” የሚለው ቃል “ድርቆሽ እንጀራ” የሚለውንም ትርጉም በውስጡ ስለሚይዝ የበለጠ አሻሚ (ambigious) ሆኖ እናገኘዋለን፡፡
ይህም ሲባል በዚህ ሐረግ ሰዎች አይግባቡበትም ማለት ሳይሆን ትክክለኛና ጥርት ያለ አስተሳሰብ ባለው ሰው የተጻፈ የጽሁፍ ሥራ መለኪያ አንባቢያን ጽሁፉን ብቻ አንብበው በቀጥታና በትክክል እንዲረዱ እንጂ በጸሐፊው አእምሮ ውስጥ የሚመላለሰውን ወይም ጸሐፊው ለመግለጽ የፈለገውን በመገመት ሞልተው እንዲገነዘቡ የማይጋብዝ መሆኑን ለማሳየት ነው፡፡
ትክክለኛ አስተሳሰብ (ሎጂክ) ወደ አንድ እውነት ወይም እውቀት ላይ ለመድረስ በሚደረገው ጉዞ ላይ ቁልፍ ቦታ አለው፡፡ ለምሳሌ በሳይንሳዊ ጥናትና ምርምር ሂደት ውስጥ ተመራማሪው የትክክለኛ አስተሳሰብ መርህን በሚገባ ካልተከተለ አንድ አዲስ ግኝት ወይም ድምዳሜ ላይ ለመድረስ አይችልም፡፡
አንድ ሃኪምም የታካሚውን ትክክለኛ በሽታ ለማወቅ መጀመሪያ ለግለሰቡ ከሚያቀርበው ቃለ መጠይቅ፣ኋላም ከቤተ ሙከራ በግለሰቡ የጤና ችግር ዙሪያ ከሚሰበስባቸው ልዩ ልዩ መረጃዎች ላይ በመንተራስ ስለታካሚው የበሽታ ምንነት አንድ ትክክለኛ እውቀት ወይም ድምዳሜ ላይ ለመድረስ መቻሉ የትክክለኛ አስተሳሰብ መርህን ጉልህ ሚና የሚያመላክት ነው፡፡
አንድ ሰው አንድን አዲስ ግኝት ወይም እውቀት እውነት ነው ብሎ ከመቀበሉ በፊት በትክክለኛ አስተሳሰብ ቀመር መነጽር በጥልቀት መመርመር ይገባዋል፡፡ አንድን ድምዳሜ እውነት ወይም ሀሰት ነው ብሎ ከመደምደሙ በፊትም እንዲሁ ስለእውነት ምንነት እውነተኛ እውቀትና ግንዛቤ ሊኖረው ይገባል፡፡ ከዚህም ባሻገር ተመራማሪው የዓለም የሳይንስ ፍልስፍና (Philosophy of Science) ሊቃውንት ስለ እውነት ምንነትና ባህርይ ያቀረቧቸውን ዘርፈ ብዙ አመለካከቶች በስፋት ሊመረምርና ከእነዚህ ውስጥም እርሱ ከተሰማራበት አውድ ጋር የሚስማማ አንድ ጥርት ያለ አመክኗዊ አቋም እንደያዘ ማረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ “እውነት አንድ ነች ወይስ ብዙ? እውነት አንጻራዊ ነች ወይስ ፍጹማዊ?፤ እውነት ጊዜያዊ ነች ወይስ ዘለዓለማዊ? እውነተኛ እውቀት ሳይንሳዊ ነው ወይስ ሃማኖታዊና ባህላዊ? ሁሉንም እውቀት የምናገኘው ከተወለድን በኋላ በስሜት ህዋሶቻች አማካኝነት በምናካብተው ገጠመኝ ነው ወይስ አብሮን የሚወለድ እውቀት አለ? እውቀት በአመክንዮና በሰብአዊ ምልከታ ይገኛል ወይስ በመለኮታዊ ኃይል ይገለጻል?” ወዘተ የሚሉትን አወዛጋቢ ሃሳቦች በአጽንኦት መርምሮ አንድ ትክክለኛ አቋም ላይ መድረስ ይኖርበታል፤ይህም ከትክክለኛ አስተሳሰብ (Logic) ውጪ የሚቻል አይሆንም፡፡
የራሳችንን ወይም የሌላን ሰው አስተሳሰብ በመገምገም ጥሩ ወይም መጥፎ አስተሳሰብ በማለት ልንፈርጀው እንችላለን፡፡ አንድን አስተሳሰብ ትክክለኛ ወይም ህጸጽ ያለበት ብሎ ለመፈረጅ ከማሳመኛ አንቀጹ (argumnet) አወቃቀርና በማስረጃነት ከቀረቡት ዓረፍተ ነገሮች የእውነታ እሴት (truth value) አንጻር በጥንቃቄ መገምገምን ይሻል፡፡ ማሳመኛ አንቀጹ ተገቢ (valid) ወይም እውነተኛ (sound) ከሆነ በድምዳሜው የተመለከተው አስተሳሰብ ትክክለኛ አስተሳሰብ ይባላል፡፡ ይሁንና ማሳመኛ አንቀጹ የማይገባ (Invalid) ከሆነ ህጸጽ ያለበት (fallacious) መሆኑ ይረጋገጣል ማለት ነው፡፡ አንድ ማሳመኛ አንቀጽ ተገቢ ነው የሚባለው ድምዳሜው ከማስረጃው ከማስረጃው(ዎቹ) በትክክል የመነጨ ከሆነ፤ ወይም የቀረቡት ማስረጃዎች በመደምደሚያው የቀረበውን ሃሳብ በትክክል ለመደገፍ የቀረቡ ከሆነ ብቻ ነው፡፡ ይሁንና ይህ ካልሆነ ወይም በአንቀጹ ውስጥ የሚገኙ ዓረፍተ ነገሮች በትክክለኛ የአስተሳሰብ ቀመር መሰረት በአመክንዮ ካልተሳሰሩ በማሳመኛ አንቀጹ የተመለከተው መደምደሚያ የተሳሳተ፤አስተሳሰቡም ህጸጽ (Fallacy) ያለበት ነው እንላለን፡
የአስተሳሰብ ህጸጽ (Logical fallacy) የሚከሰተው በማሳመኛ አንቀጽ ላይ የቀረበው መደምደሚያ ከቀረቡት ማስረጃዎች በተገቢ (valid) መንገድ ያልወጣ ከሆነ ነው፡፡ አንድ መደመደሚያ ከማስረጃው በተገቢ መንገድ አልወጣም የሚባለው ግለሰቡ ድምዳሜውን ለመስጠት ያቀረባቸው ማስረጃዎች በመደምደሚያው ላይ ለቀረበው ይዘት አመክኖያዊ አስፈላጊነት የሌላቸው ከሆኑ፣በማሳመኛነት የቀረበው ምስስሎሽ (Analogy) ደካማ ከሆነ፣ ማሳመኛው ግልጽነት በጎደለው ሁኔታ አሻሚ (ambigious) ቃላትን በመጠቀም የተገነባ ከሆነ፣ በማሳመኛው የቀረበው ድምዳሜ በቀጥታ ከማስረጃዎቹ የመነጨ ሳይሆን የግለሰቡን አመለካከትና ፍላጎት የሚያንጸባርቅ ከሆነ እንዲሁም በጽሁፍ ውስጥ በስዋስው የትርጉም ምስስሎሽ ስህተት የተሳሳተ ድምዳሜ ከተሰጠ ነው፡፡

No comments: