Friday, March 8, 2013

ቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሴ[1897 - 1939]


                                 ቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሴ[1897 - 1939]


" ኮከብ እምኮከብ ይኄይስ ክብሩ" የሚል የኖረ የግእዝ አባባል አለ:: አንዱ ኮከብ በብርሀኑ፤ በግዘፉ፤ መጠቅላላ ተፈጥሮው ከሌላው ኮከብ ይበልጣል:: እኔን የሚያስገርመኝ ይኽ አይደለም:: እንዳንድ ከዋክብት አሉ--በተለየ አጠራር ተወርዋሪ የምንላቸው:: በሌሊቱ ኅዋ ውስት ከአንዱ መአዘን ሰማይ ወደ ሌላው ተወርውረው ብልጭ ብለው ይጠፋሉ:: ይህ ሁሉ የሚሆነው በቀፅበት ነው::ያንን በጨለማው ግርማ የተዋጠውን ኅዋ በብርሃን ጎርፍ ሰንትቀው አጥለቅልቀውት ይጠፋሉ:: ተመልካችም ከመገረም በሚመነጭ ዝምታ ይዋጣል:: በኢትዮዽያም የሥነ ጽሑፍ ኅዋ ውስጥ ዮፍታሔ ንጉሤ አንድ ተወርዋሪ ኮከብ ነበር።

ብሩህ ነጸብራቁ፤
ውበቱና ድምጹ አንድነት ተሰማ
ተው አንድነት ቢበርቁ፤ የመያው
ቅለት ጠፍቶ፤ ምስጢሩን አካቶ፤
ተወርዋሪ ኮከብ በራሱ ነበልባል
በራሱ ነዲድ ተቃጥሎ የጠፋ፤
ተወርዋሪ ኮከብ በምናየው ሰማይ
ነበረ በይፋ።


አዎን፤ ነበረ። በዚያን ቅጽበት በሆነው የጽሁፍ ዘመን ዮፍታሔ፤ የኢትዮዽያን የስነጽሁፍ ኅዋ በቅኔ ፤ በግጥም ፤በመዝሙርና በተውኔት የብርሃን ጎርፍ ሰንጥቆ አጥለቅልቆት ጠፍቷል። ዛሬ የሚያሳዝነው የዚህ ተወርዋሪ ኮከብ ተጽእኖ በዘመናችን መጥፋቱ ነው።

ስለ ዮፍታሔ ንጉሴ በሕፃንነቴ እናት አባቴ ሲያወጉ፤ ሲወያዩ፤ አንዳንዴም ሲከራከሩ እሰማ ነበርበተለይ አባቴ ከዮፍታሔ ንጉሴ ተውኔቶችና መዝሙሮች በቃሉ የሚያስታውሳቸውን ስንኞች ሲያንጎራጉር እየሰማሁ የዮፍታሔ ፍቅር በሕፃን ልቦናዬና ስሜቴ ተሳለብኝ ። ያኔ ከሰማኋቸው ትዝ የሚሉኝ "አንተ ባ...ጎራዴ ግዛ" እና "ወላድ ኢትዮዽያ ለልጆቻ ብላ እጅግ ሳይትሩባት ሳይዘሯት አብቅላ" የተባሉት መዝሙሮች ናቸው። ሁለተኛው በጣም ጠሊቅ መዝሙር ነው። ጠሊቅነቱ የተገነዘብሁት ካደግሁ በኋላ ነው። ያኔ መዝሙሩ ይመስጠኝ የነበረው በቃላቱ ጣእመ ዝማሬ ነበረ። የፊተኛውን መዝሙር ግጥሙን በሙሉ ላገኘው አልቻልሁም። የኋለኛው ግን "ብርሃንና ሰላም" ይባል በነበረው ጋዜታ በሙሉ ተጽፎ ስላገኘሁት ከዚህ ቀጥሎ ጽፌዋለሁ፤

ወላድ ኢትዮዽያ ለልጆቿብላ፤
እጅግ ሳይጥሩባት ሳይዘሯት አብቅላ፤
ስንዴውን ጠብቃ እንክርዳዱን ነቅላ፤
ስትመግበን አየን በፀሐይ አብስላ።



ምሳሌ ዘርእ አገራችን፤
ንጹሕ ዝናብ መንግሥታችን።
በመልካሙ ዘርእ ላይ እንክርዳቸ ሲዘራ፤
ታሳድገውና ከእንክርዳዱ ጋራ፤
ገለባ ሲቃጠል ገበሬ ሲያመራ፤
ታቃጥለዋልች እንክርዳዱን አብራ።
ምሳሌ ዘርእ አገራችን፤
ንጹሕ ዝናም መንግስታችን ።
አይዞህ የኛ ጌታ ነገርህን አትርሳ፤
አለስልሰህ ዝራ የስንዴውን ማሳ፤
የተዘራችው ዘርእ ፈርሳና በስብሳ ፤
ታፈራልቸ ፍሬ ሙታ ስትነሣ።
ምሳሌ ዘርእ አገራችን፤
ንጹሕ ዝናም መንግስታችን ።
በጊዜው የዘራ መልካም ዘር አትርፎ፤
ከበሮቹ ጋራ ማታ ከትላ አርፎ፤
ብርነት ታትቆ በቅን ተሰልፎ፤
በቸርነት ታጥቆ በቅን ተሰልፎ፤
ደግሞ ዘሩን ዘራ መክር አሳልፎ።
ምሳሌ ዘርእ አገራችን፤
ንጹሕ ዝናም መንግስታችን ።



ኋላም ትምህርት ቤት ከገባው በኋላ፣ በተለይም መሁለተኛ ደረጃ በነበርሁበት ጊዜ ፣ በብላታ መርስዔ ሐዘን ስዋስው ውስጥ የዮፍታሔ ቅኔዎች፣ ግጥሞችና መዝሙሮች አልፎ አልፎ ተጠቅሰው በማግኘቴ በቃሌ አትንቼ እንደ ዳዊት እደግማቸው ነበረ። መጀመሪያ ምናቤን የመታው ፤ ስሜቴን የነካው የዮፍታሔ የቋን ቋው ኀይልና ውበት ነበር።ኋላም ስለ ቅኔም ሆነ ስለግጥም አንዳንድ ነገር ከገረጫጨፍሁ በኋላ ያን መጀመሪያ ምናቤን የመታውን፣ ስሜቴን የነካውን የቋንቋ ኀይልና ውበት መመርመር ጀመርሁ። የዮፍታሄ ስንኞች መቀነባበር፤ የዘይቤው ወይንም የስለምኑ መተባበርና መዋሐድ ፤ በስተቅኔውም በኩል የሰምና ወርቁነ፤ የውስተ ወይራው፤ የሰም ለበሱ ፤ የኅብሩና የምርምሩ አካሄድ እስከ ዛሬ ከተነሱት ገጣሚዎች ሁሉ ዮፍታሔን የተለየ ያደርጉታል። የዮፍታሔ ርቀቱ ፤በኪነት ሥራው ሁሉ ከሀብተ ትንቢት ጋር የተሳላው የዘይቤው ወይንም የስለምን ስልቱ ልዝብ በመሆኑ አይኮሰልም፤ ወይንም ሌላ ሊቀዳው አይችልም። ወጥነቱ የተመሠረተው በዚህ ላይ ነው። ---ንጹሕ የኪነት ወጥነት ነው።

No comments: