Thursday, March 14, 2013

የአምላክን መኖር በፍልስፍና ማረጋገጥ ይቻላልን?

አንዱ መልካም ነገር ከሌላው መብለጡ ግድ ከሆነና ከላይ የተመለከትናቸው ነገሮች መልካምነት አንጻራዊ ነው ከተባለ ከመልካም ነገሮች ሁሉ የላቀ መልካም የሆነ፣ ለመልካምነቱ አቻ የሌለው መልካምነቱም ከራሱ የመነጨ (Intrisitic) አንድ አካል አለ ብሎ መደምደም አመክኗዊ ይሆናል፡፡ መልካም ነገሮች ሁሉ እንደሚወደዱ ሁሉ ይህ የመልካሞች ሁሉ መልካም (Supreme Good) የሆነ ታላቅ አካል ከመልካሞች ሁሉ የበለጠ ሊወደድ ይገባል ማለት ነው፡፡
የሚታየውንና የማይታየውን ዓለም (universe) ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣ፣ የሚቆጣጠር፣ ከሰው ልጆች እውቀትና ኃይል በላይ የሆነ አምላክ (God) የሚባል ላዕላይ ነገር (Being) የመኖሩ ወይም ያለመኖሩ ጥያቄ የዓለም ጠቢባንን ለበርካታ ዘመናት ሲያስጨንቅ የሰነበተና ዛሬም ድረስ ብዙዎችን በማወዛገብ ላይ የሚገኝ ዓቢይ ጥያቄ ነው፡፡ ለመሆኑ አምላክ አለ? መኖሩን ወይም አለመኖሩን ማረጋገጥ ይቻላል? እንዴት? በእምነት ብቻ? በፍልስፍና ? በሳይንስ? በእምነትና በፍልስፍና? መልሱ እንደየዘመናቱና እንደየመላሾቹ ግለሰቦች ማንነት ሃማኖታዊ፣ ሳይንሳዊ ወይም ፍልስፍናዊ መልክ ሊኖረው ይችላል፡፡
ሃይማኖታዊው ምላሽ የአምላክን ህልውና በቅዱሳት መጻህፍት
ምስክርነት (Scriptural truth) ወይም በምስጢራዊ መገለጽ (revelation) ማረጋገጥ ስለመቻሉ ሲያስረግጥ፤ ሳይንሳዊው ምልከታ ደግሞ የአምላክ ህልውና ጥያቄ በሳይንሳዊ መንገድ ሊረጋገጥ የሚችል (verifiable) አይደለም ይላል፡፡ የፍልስፍናን አተያይ ስንመለከት በአንድ በኩል በርካታ ፈላስፎች (theists) የአምላክን ህልውና በፍልስፍና ማረጋገጥ ይቻላል የሚል እምነት ሲያራምዱ ሌሎች ደግሞ (Atheists) በተቃራኒው ስለአምላክ አለመኖር በፍልስፍና ማረጋገጫ መስጠት ይቻላል በሚል በሁለት ጎራ ተከፍለው ለዘመናት ተከራክረዋል፤ አስተምረዋል፤ ጽፈዋልም፡፡
ከዚህም ባሻገር የአምላክን ሆነ የሌሎች መንፈሳዊ አካላትን ህልውና ማረጋገጥ ወይም ስለመኖራቸውም ሆነ ስላለመኖራቸው እርግጠኛ መሆን በጭራሽ አይቻልም የሚል አስተሳሰብ የሚያራምዱ ጎኖስቲካዊ አመለካከት ያላቸው ፈላስፎች (agnostics) ማዕከላዊ የሆነ አቋም ይዘው ሁለቱ ጽንፎች ሲያቀራርቡ ኖረዋል፡፡ በዚህ ክፍል ላይ “የአምላክን ህልውና በፍልስፍና ማረጋገጥ ይቻላል!” የሚለውን የፍልስፍና መስመር ተከትለው የቅዱሳት መጻህፍትን ምስክርነት ሳይሹ በአመክንዮ (reasoned argument) ላይ ብቻ ተመስርተው ለአምላክ ህልውና ፍልስፍናዊ ማረጋገጫ የሰጡ ፈላስፎችን ስራ ለማየት እንሞክራለን፡፡
የፈጣሪን ህልውና ከሚቀበሉና የአምላክን ህልውና በአመክንዮ ማረጋገጥ ይቻላል ብለው ከተከራከሩ ፈላስፎች መሃል አንሰልም፣ አኳይናስ፣ ኦውግስቲን ከክርስትናው፤ እንዲሁም አቬሲናና አቬሮስ ደግሞ ከእስልምናው ዓለም በአብነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ አምላክ (God) የሚለው ቃል በበርካታ ፈላስፎች ስራዎች ውስጥ የምናገኘው ቃል ቢሆንም ቃሉን የተለያየ ሃሳብን ለመግለጽ ተጠቅመውበታል፡፡ ለምሳሌ ቴሊስ ውሃን፣ ሬኔ ዴካርት አምላክን፣ እንዲሁም አንሰልም፣ አኳይናስና ኦውግስቲን ደግሞ እግዚአብሔር የሚለውን ቃል ለማመልከት ተጠቅመውበታል፡፡
አንሰልም ከ1033-1109 ዓ.ም የነበረ ጣልያናዊ የስነመለኮት ምሁርና ፈላስፋ ሲሆን Monologion እና Proslogion በተባሉ ስራዎቹ የእግዚአብሄርን ህልውና ማረጋገጫ ፍልስፍና (ontological argument) ያቀረበ ነው፡፡ የአንሰልም የማረጋገጫ ፍልስፍና መዋቅር (framework) በአመክንዮ ላይ የተመሰረተ እምነት (reasoned faith) አንዲኖር የሚያስረግጥ ሲሆን ይህም እምነትን (faith) ከአመክንዮ (reason) የሚያስቀድመውን ነባር አስተሳሰብ የሚቃረን ነው፡፡ እንደ አንሰልም እምነት የክርስትና እምነት ዶግማ በአመክንዮ ላይ የተመሰረተ ነው፡፡
ምክንያቱም አምላክ ራሱ በላዕላይ አመክንዮ (supreme reason) የሚመራና በፈጠራቸው ፍጥረታት ላይ ይኸው ጥበቡ የሚገለጽ በመሆኑ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር የሰው ልጆች ሁሉ አመክንዮ ከአምላክ የተሰጣቸው ስለሆኑና የእምነት መነሻ ምክንያትን መገንዘብ ስለሚችሉ አስቀድመው ህልውናውን የሚያምኑ ክርስቲኖችም ሆነ በቅዱሳት መጻህፍት የማያምኑ ግለሰቦች ሁሉ የእግዚአብሔርን ህልውና በአመክንዮ ላይ ብቻ ተመስርተው ማረጋገጥ ይችላሉ፡፡ አንሰልም ካቀረባቸው እርስ በርሳቸው የተያያዙ ሶስት ማረጋገጫዎች መካከል የመጀመሪያው ያደረገው በዓለም ካሉ ጥሩ ነገሮች ሁሉ የበለጠ አንድ ጥሩ ነገር (Supreme Good) መኖሩን ማረጋገጥ ነው፡፡ በመቀጠልም ይህንንም ማረጋገጫ ተንተርሶ ከሁሉም በላይ የሆነ ባህርይ ያለው (Supreme Nature) አካል መኖሩን ማረጋገጥ፤ በመጨረሻም በሁለተኛው ማረጋገጫ ላይ ተመርኩዞ በሁሉም ነገር ከሁሉም የበለጠ አካል (Most Excellent Being) ወይም አምላክ መኖሩን በማረጋገጥ ይደመድማል፡፡
የአንሰልም የመጀመሪው ማረጋገጫ የመልካሞች ሁሉ መልካም የሆነ ነገር (Supreme Good) ስለመኖሩ ነው፡፡ በዓለማችን ላይ በርካታ ጥሩ ነገሮች አሉ፡፡ የጥሩነታቸውን መጠን ስናወዳድር ግን ጣት ከጣት ይበልጣል እንደሚባለው አንዱ ጥሩ ነገር ከሌላው መብለጡ የግድ ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ ፈረስ ከሌላው፤ መልካም ፈረስ የሚባለው ከጥንካሬውና ከፍጥነቱ አንጻር ነው፡፡ ይሁንና ጠንካራና ፈጣን የሆነ ዘራፊ ግን መልካም ሰው ሊባል አይችልም፤ መጥፎ እንጂ፡፡ በመሆኑም አንጻራዊ የሆነ መልካምነት (Good) ያላቸው ነገሮች በራሱ (Intrisitically) መልካም ከሆነ ነገር አንጻር ያነሰ መልካምነት ያላቸው ነገሮች ናቸው፡፡ በሌላ አነጋገር መልካም እንጨት፣ መልካም ፈረስ፣ መልካም ሰው ሁሉም በመጠኑ መልካም የሆኑ ነገሮች ናቸው፡፡ መልካም ናቸው ብለን በደመደምንበት መስፈርት አሰሳ ብናካሂድ ለእነርሱ አቻ የሆኑ ሌሎች መልካም ሰዎች፣ ፈረሶችና ሰዎችን መዘርዘር እንችላለን፡፡
ነገር ግን መልካም እንጨት ከመልካም ፈረስ ወይም ከመልካም ሰው ጋር አንድ ዓይነት የመልካምነት ባህርይ ስለሌላቸው የአንዱን መልካምነት ከሌላው ጋር ማወዳደር ትክክል አይሆንም፤ ሁሉም ከአቻዎቻቸው ጋር ይነጻጸራሉ እንጂ፡፡ በመሆኑም አንዱ መልካም ነገር ከሌላው መብለጡ ግድ ከሆነና ከላይ የተመለከትናቸው ነገሮች መልካምነት አንጻራዊ ነው ከተባለ ከመልካም ነገሮች ሁሉ የላቀ መልካም የሆነ፣ ለመልካምነቱ አቻ የሌለው መልካምነቱም ከራሱ የመነጨ (Intrisitic) አንድ አካል አለ ብሎ መደምደም አመክኗዊ ይሆናል፡፡ መልካም ነገሮች ሁሉ እንደሚወደዱ ሁሉ ይህ የመልካሞች ሁሉ መልካም (Supreme Good) የሆነ ታላቅ አካል ከመልካሞች ሁሉ የበለጠ ሊወደድ ይገባል ማለት ነው፡፡ የአንሰልም ሁለተኛው ማረጋገጫ ከሁሉም በላይ የሆነ (ልዑል) ባህርይ ያለው አካል (Supreme Nature) ስለመኖሩ የሚያትት ነው፡፡ በዓለማችን ላይ የሚገኙ የሚታዩና የማይታዩ ነገሮች ካለመኖር ወደመኖር ሲመጡ ወይ ከሆነ ነገር (out of something) ተገኝተዋል አልያም ከምንም (out of nothing) የተገኙ ናቸው፡፡ በሳይንሳዊው ሮጀርስ መርህ ደግሞ “Nothing comes from nothing” ከምንም የተገኘ ምንም ነገር የለም፡፡
ስለሆነም በዓለማችን ላይ የሚገኙ ነገሮች ሁሉ የተገኙት ከሆነ ነገር (something) ነው ማለት ነው፡፡ ዓለማችን ከሆነ ነገር ተገኝታለች ብለን ካመንን የሚታዩና የማይታዩ ነገሮች ሁሉ የተገኙት ወይ ከአንድ ነገር ነው አልያም ከብዙ ነገሮች ነው ማለት ነው፡፡ ዓለማችን የተገኘችበት ብዛት ያላቸው ነገሮች ካሉ ለእነዚህ ነገሮች ሁሉ አንድ ብቸኛ አስገኚ አላቸው፤ አልያም እንዳንዱ ነገር በራሱ የተገኘ ነው፤ወይም ደግሞ አንዱ ከሌላው የተገኘ ነው፡፡ እያንዳንዱ ነገር በራሱ የተገኘ ነው እንዳንል ምንም ነገር ከምንም ሊገኝ አይችልም፡፡ አንዱ ከሌላው የተገኘ ነው ብንልም አስገኚውን ነገር ያስገኘውን ሌላ አስገኚ ማግኘት ግድ ይለናል፡፡ ይህም ብዛት ያላቸውን ነገሮች ያስገኘ፤ በራሱ የተገኘ አንድ ኃይል አለ ወደሚለው ድምዳሜ ያስገባናል፡፡ ብዛት ያላቸው ነገሮች የተገኙበት አንድ አካል አለ ማለት የሚታዩና የማይታዩ ነገሮች በሙሉ የተገኙት በራሳቸው ሳይሆን ከእነርሱ ውጪ በሆነ አካል ነው ማለት ነው፡፡
ከራሱ ውጪ በሆነ አካል የተገኘ ነገር በሙሉ በራሱ ከተገኘ ነገር አንጻር ዝቅተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ወይም ያነሰ ነው፡፡ ስለዚህ በራሱ ከተገኘው አካል ውጪ ያሉ ነገሮች በሙሉ በባህርያቸው በራሱ ከተገኘው አካል ያነሱ ናቸው፡፡ ከዚህም በመነሳት በራሱ የተገኘው አካል ታላቅና (Great) ከሁሉም በላይ የሆነ (ልዑል) ባህርይ (Supreme Nature) አለው ማለት ነው፡፡ ይህም አንሰልም ከሁሉም በላይ እጅግ በጣም መልካም የሆነ አካል (Excellent Being) ስለመኖሩ የሚያትተውን ሶስተኛ ማረጋገጫ ያስከትላል፡፡ እንደ ሰር ጀምስ ፍሬዘር ብያኔ አምላክ ማለት የመጀመሪያው ኃያል አስገኚ፣ ዓለምን የሚቆጣጠር፣ ከሰዎች እውቀትና ከተፈጥሮ ህግ በላይ የሆነ አካል ነው፡፡ እንደ አንሰልም እምነት አምላክ ማለት ከእርሱ በላይ ማንም ምንም ኃያልና መልካም ቀዳሚ የሌለ አካል ማለት ነው፡፡
የዚህ ዓይነት አካል (Being) ስለመኖሩ በእእምሮአችን ውስጥ ሊታሰብ ይችላል፤ በሁለተኛው ማረጋገጫ የተመለከተውን ከሁሉም በላይ የሆነ (ልዑል) ባህርይ ያለው አካል (Supreme Nature) በመኖሩ የተስማማ ሰው፣ በትክክለኛ የአስተሳሰብ ቀመር (Logic) ስሌት መሰረት ይህ አምላክ አለ ብሎ መደምደሙ ተገቢ ይሆናል፡፡ ስለአምላክ ህልውና በሁለተኛ ደረጃ የሚገኘው የፈላስፎች ማረጋገጫ ከስነፍጥረት አንጻር የቀረበ ማሳመኛ (cosmological argument) ነው፡፡ በመካከለኛው ዘመን የነበረው የቶማስ አኲናስና በ18ኛው ክፍለ ዘመን የተነሳው ሳሙኤል ክላርክም ስራዎች ለዚህ ፍልስፍና ማሳያዎች ናቸው፡፡
አኲናስም ሆነ አብዛኞቹ የዚህ ፍልስፍና አራማጆች የሚያቀርቡት ማሳመኛዎች የሚከተለውን የአመክንዮ መዋቅር የተከተለ ነው፡፡ ማንም ሰው ስነ-ፍጥረትን ወይም በጊዜና በቦታ ተወስኖ የሚታየውና የማይታየውን ዓለም ህልውና ይገነዘባል፡፡ ይህ ዓለም ደግሞ ራሱን በራሱ አስገኘ ማለት አይችልም፡፡ ይህ እጅግ በጣም ውስብስብ የሆነ ዓለም ከምንም ተገኘ ማለት ደግሞ አይቻልም፡፡ ከሌላ ከሆነ ግዑዝ ነገር ተገኘ ካልን የመጨረሻውን አስገኚውን ለማግኘት መጨረሻ ወደሌለው የአስገኚና የተገኚ ክትትሎሽ ውስጥ እንገባና ያለመልስ እንቀራለን፡፡ ስለዚህ ይህ ዓለም ከጊዜና ከቦታ ውጪ በሆነ ያልተገኘ ግን የሚያስገኝ አንድ የመጨረሻ አካል የተገኘ ነው፡፡ በዚህ ፍልስፍና በቀዳሚነት የሚታወቀው ጣልያናዊው ፈላስፋና የሥነ-መለኮት ምሁር ቅዱስ ቶማስ አኲናስ (1225-1274) “Summa Theologiae” በተባለ መጽሐፉ የፈጣሪን ህልውና በአምስት መንገድ ሊረጋገጥ እንደሚችል አስረድቷል፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ማንም ሰው ለማየትና ለማረጋገጥ እንደሚችለው በዓለም ላይ የሚገኙ የተወሰኑ ነገሮች ሁልጊዜ በእንቅስቃሴ ላይ ናቸው፡፡
ማንኛውም ተንቀሳቃሽ ነገር የሚንቀሳቀሰው በሌላ አንቀሳቃሽ ነው፤ ምክንያቱም እንቅስቃሴ የሚፈጠረው አንድን የመንቀሳቀስ አቅም (potentiality) ያለውን ነገር ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ (actuality) መለወጥ የሚችል ኃይል ሲኖር ብቻ ነው፡፡ አንድና ተመሳሳይ ነገር ደግሞ በራሱ አንቀሳቃሽም ተንቀሳቃሽም መሆን አይችልም፡፡ ለምሳሌ እንጨት የሚፋጅ ሞቃት የመሆን አቅም አለው ነገር ግን ወደሞቃትነት የሚለወጠው እሳትን ሲያገኝ ብቻ ነው፡፡ ስለሆነም ማንኛውም የሚንቀሳቀስ ነገር የግድ በሌላ ሊንቀሳቀስ ይገባል ማለት ነው፡፡ አሁን የምናያቸው የሚንቀሳቀሱ ነገሮች በቅርብ የምናውቀው አንቀሳቃሽ ቢኖራቸውም ለዚያ አንቀሳቃሽ ሌላ አንቀሳቃሽ አለው፡፡
ይህም በመጨረሻው ወደ መጀመሪያው አንቀሳቃሽ እርሱ ግን በሌላ በማንም ወደማይንቀሳቀሰው አንቀሳቃሽ ያደርሰናል፤ እርሱን ሁሉም አምላክ ብለው ይረዱታል፡፡ ሁለተኛ በዚህ በሚታየው ዓለም የምክንያትና (cause) የውጤት (effect) ትስስር ስርዓት እናያለን፤ አንዱ ነገር ቀጥተኛ ምክንያት (efficient cause) ሆኖ ሌላኛውን ሲያንቀሳቅሰው ማለት ነው፡፡ ለአንድ ውጤት አንድ ወይም ከአንድ በላይ ምክንያቶችን በመሃል ላይ ልናገኝ እንችላለን፡፡ እነዚህ ማዕከላዊ ምክንያቶች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ አሁንም አንዱ ምክንያት ሌላውን አስገኘ እያልን ብንቀጥል የትየለሌ (infinity) ውስጥ እንገባለን፤ ይህም መልስ አይሆንም፡፡ ስለዚህም አንድ የመጀመሪያ ቀጥተኛ ምክንያት (first efficient cause) መኖሩን መቀበል ግድ ይለናል፤ ይህም አምላክ የሚል መጠሪያ የተሰጠው ነው፡፡ በሌላ በኩል በዓለም ላይ ያሉ ነገሮችን ስንመለከት፣ እንዴት ሊሆን ቻለ (How possible) ብለን እንጠይቃለን፤ ነገሮቹን ሊኖሩ ወይም ላይኖሩ ይችሉ ነበርና፡፡ ነገሮችን ካለመኖር ወደ መኖር በማምጣት ረገድ ምንም እንኳ በርካታ መካከለኛ ምክንያቶችን ብንመለከትም በመጀመሪያ የግድ አንድ በራሱ የተገኘ ኃይል (necessity) ሊኖር እንደሚገባ የታመነ ነው፡፡ ከዚህም ሌላ የተፈጥሮን ሥርዓት ደረጃ (gradation) ስንመለከት አንዱ ነገር ከሌላው የበለጠ ወይም ያነሰ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ በአንድ ዋና ምድብ (genus) ውስጥ የምናገኘው የመጨረሻው ነገር የምድቡ አስገኚ ነው፡፡
እሳት የሞቃት ነገሮች ምድብ የመጨረሻው ደረጃ እንደመሆኑ መጠን የሞቃት ነገሮች ሁሉ አስገኚ ነው፡፡ ስለዚህም ከጎዶሎነት ወደ ፍጹምነት ካለማወቅ ወደ ጠቢብነት ከፍ እያልን ስንመጣ የምናገኛቸው የመጨረሻ የፍጹማን ፍጹም፣ የመልካሞች ሁሉ መልካም፣ የጠቢባን ሁሉ ጠቢብ የምክንያቶች ሁሉ ምክንያት አምላክ ብለን የምንጠራው ነው፡፡ በመጨረሻም ከዓለም አስተዳደር (governance of the world) የቀረበውን ማሳመኛ ስንመለከት፣ በሚሰራው ስራ ዙሪያ እውቀት ያነሰው ማንኛውም አካል የተሻለ እውቀትና ጥበብ ባለው ሌላ አካል ካልታገዘ ወይም ካልተመራ በቀር ውጥኑን ከግብ ለማድረስ እንደማይችል ሁሉ ይህቺን ዓለምና በውስጧ ያሉ ነገሮች የተፈጠሩበትን ዓላማ ግብ መምታት እንዲችሉ ዓለምን በዓላማና በጥበብ የሚመራ አንድ እጅግ አዋቂና ጠቢብ አካል (intelligent being) አለ ብሎ ማመን ተገቢ ይሆናል፡፡ ስለአምላክ ህልውና በሶስተኛ ደረጃ የቀረበው (Teleological Argument) በመባል የሚታወቀው ሲሆን ይህም አኲናስ በመጨረሻ ደረጃ ካስቀመጠው ማረጋገጫ ጋር የሚቀራረብ ነው፡፡
የዚህ ማሳመኛ ዋና የፍልስፍና መዋቅር፣ ይህቺ ዓለም ያለ አንድ ዓላማ (purpose)፣ ግብና (goal) አስገኚ (designer) በዘፈቀደ የተገኘች አለመሆኗን ማረጋገጥ ነው፡፡ የዊሊያም ፓሊ (William Paley) 1743-1805 የእጅ ሰዓት ምሳሌ (watch analogy) ማሳመኛ በዚህ ረገድ ቀዳሚውን ስፍራ የያዘ ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ የእጅ ሰዓት መሬት ላይ ወድቆ ቢገኝ፣ መሬት ላይ ወድቆ እንደተገኘ ድንጋይ እንዲሁ ያለዓላማና ያለአስገኚ ተገኘ ብለን ማሰብ አይገባንም፤ ምክንያቱም የተገኘው ሰዓት አንድ በሰዓት ምህንድስና ጥበብ በተካነ መሃንዲስ (designer) በጥንቃቄ በውስጡ ያሉት ልዩ ልዩ ጥርሶችና ተገጣጣሚ አካላት እርስ በርስ ተቀናጅተው በቀን አስራ ሁለት ሰዓት፣ በሰዓትና በደቂቃ ደግሞ ስልሳ ጊዜ እየተሽከረከረ ሳይዛነፍ በትክክል ጊዜን ለመለካት ዓላማ የተሰራ ነው፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ በዓለም ውስጥ የሚገኙ እጅግ ውስብስብና አስደናቂ በሆነ መንገድ እርስ በርሳቸው የተሳሰሩ ነገሮች ለምሳሌ ረቂቅና ግዙፍ፣ እንስሳትና ዕጽዋት፣ ፀሐይና ጨረቃ፣ አንጎልና ልብ፣ አጥንትና ጅማት፣ፕላኔቶችና ምህዋሮቻቸው የመሳሰሉት ነገሮችም እንዲሁ ያለዓላማና ያለአስገኚ በዘፈቀደ ተገኙና የሚሰሩ ናቸው ብሎ ማሰብ ስህተት ይሆናል፡፡ ሰዓቱን የሰራውን መሃንዲስ ማንነት በትክክል አለማወቃችን ለሰዓቱ አስገኚ የለውም ለማለት እንደማያበቃን ሁሉ የአምላክን ማንነት በትክክል አለመረዳታችንም ለዚች ዓለም አስገኚና መጋቢ አምላክ የላትም፤ እንዲሁ የተገኘች ናት ለማለት በቂ ምክንያት አይሆንም ማለት ነው፡፡ እስከ አሁን ከተመለከትናቸው የፈጣሪ ህልውና ማሳመኛዎች በተለየ መልኩ የምናገኘውና የአንዳንድ ግኖስቲክ ፈላስፎች አቋም ከሆነው ፍልስፍና አንዱ የፓስካል ዌይጀር (Pascal’s Wager) ማሳመኛ በመባል ይታወቃል፡፡
እንደ አስራ ስድስተኛው ክፍለ ዘመን ፈረንሳዊው ፈላስፋና ሳይንቲስት ብሌይዝ ፓስካል እምነት አምላክ አለ ወይም የለም ብሎ በርግጠኝነት መናገር አይቻልም፡፡ ፍልስፍናም ሆነ ሳይንስ ለርግጠኝነታችን ድጋፍ ማቅረብ አይችሉም፡፡ በአምላክ ህልውና ጥያቄ ውስጥ እንደ ውርርድ ቁማር (Wager) የተሻለ ያዋጣል ብለን የምናስበውን አቋም ደግፈን በተስፋ ከመጠባበቅ የተሻለ ምርጫ አይኖረንም፡፡ እርግጠኛ ባልሆንበት ሁኔታ አምላክ የለም የሚለውን አቋም ብንይዝና ግምታችን የተሳሳተ ቢሆን ከፍተኛ ዋጋ እንከፍላለን (infinite suffering) ግምታችን ትክክል ሆኖ ቢገኝ ግን የምናገኘው ዋጋ ግን በዘመን የተወሰነ ምድራዊ ደስታ (finite earthly happiness) ነው፤ ነገር ግን እርግጠኛ ባንሆንም እንኳ አምላክ አለ የሚለውን አቋም ብንደግፍ ግምታችን ትክክለኛ ሆኖ ከተገኘ የምናገኘው ሽልማት እጅግ ከፍ (infinite salvation) ሲሆን የምናጣው እጅግ በጣም አነስተኛ ነገር ነው፡፡ በውርርድ ቁማር ውስጥ ከተሸነፍክ ያስያዝከውን ነገር በሙሉ ታጣለህ፤ ካሸነፍክ ግን ምንም የምታጣው ነገር አይኖርም፡፡ “If you win you win everything, if you lose you lose nothing.” ስለሆነም በአመክንዮ ለሚመራ ሰው በአምላክ ህልውና ካለማመን ይልቅ ማመን የተሻለ ነው፡፡

No comments: